ምዕራፎች

  1. 1
  2. 2
  3. 3
  4. 4
  5. 5
  6. 6
  7. 7
  8. 8
  9. 9
  10. 10
  11. 11
  12. 12
  13. 13
  14. 14
  15. 15
  16. 16
  17. 17
  18. 18
  19. 19
  20. 20
  21. 21
  22. 22
  23. 23
  24. 24
  25. 25
  26. 26
  27. 27
  28. 28
  29. 29
  30. 30
  31. 31
  32. 32
  33. 33
  34. 34
  35. 35
  36. 36
  37. 37
  38. 38
  39. 39
  40. 40
  41. 41
  42. 42

ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ኢዮብ 39 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

1. “የበረሃ ፍየል የምትወልድበትን ጊዜ ታውቃለህን?ዋልያ ስታምጥስ ተከታትለህ አይተሃል?

2. የእርግዝናቸው ወራት ምን ያህል እንደሆነ ትቈጥራለህን?የሚወልዱበትንስ ጊዜ ታውቃለህን?

3. ተንበርክከው ይወልዳሉ፤ከምጣቸውም ጣር ይገላገላሉ።

4. ግልገሎቻቸውም ይጠነክራሉ፤ በሜዳም ያድጋሉ፤ተለይተው ይሄዳሉ፤ ወደ እነርሱም አይመለሱም።

5. “ለሜዳ አህያ ነጻነት የሰጠው ማን ነው?እስራቱንስ ማን ፈታለት?

6. ምድረ በዳውን መኖሪያው፣የጨውንም ምድር ማደሪያው አድርጌ ሰጠሁት።

7. በከተማ ውካታ ይሥቃል፤የነጂውንም ጩኸት አይሰማም።

8. በየተራራው ይሰማራል፤ሐመልማሉንም ሁሉ ለማግኘት ይወጣል።

9. “ጐሽ ያገለግልህ ዘንድ ይታዘዛልን?በበረትህስ አጠገብ ያድራልን?

10. እንዲያርስልህ ልትጠምደው ትችላለህ?ወይስ እየተከተለህ ዕርሻህን ይጐለጒልልሃልን?

11. ጒልበቱ ብርቱ ስለ ሆነ ትተማመንበታለህ?ከባዱን ሥራህንስ ለእርሱ ትተዋለህ?

12. እህልህን እንዲሰበስብልህ፣በዐውድማህም ላይ እንዲያከማችልህ ታምነዋለህን?

13. “ሰጎን ክንፎቿን በደስታ ታራግባለች፤ነገር ግን እንደ ሽመላ ላባዎች ሊሆኑ አይችሉም።

14. ዕንቍላሏን መሬት ላይ ትጥላለች፤እንዲሞቅም በአሸዋ ውስጥ ትተወዋለች።

15. እግር እንደሚሰብረው፤የዱር አውሬም እንደሚረግጠው አታስብም።

16. የእርሷ እንዳልሆኑ ሁሉ በልጆቿ ትጨክናለች፤ድካሟም በከንቱ ቢቀር ደንታ የላትም፤

17. እግዚአብሔር ጥበብ ነሥቶአታልና፤ማስተዋልንም አልሰጣትም።

18. ለመሸምጠጥም ክንፎቿን ስትዘረጋ፣በፈረስና በጋላቢው ትሥቃለች።

19. “ለፈረስ ጒልበትን ትሰጠዋለህን?ዐንገቱንስ ጋማ ታለብሰዋለህን?

20. እንደ አንበጣ የምታስዘልለው አንተ ነህን?የማንኰራፋቱም ገናናነት አስፈሪ ነው።

21. በጒልበቱ እየተመካ በብርቱ ይጐደፍራል፤ጦርነት ሊገጥም ይወጣል።

22. ያለ አንዳች ሥጋት፣ በፍርሀት ላይ ይሥቃል፤ሰይፍ ቢመዘዝበትም ወደ ኋላ አይልም።

23. ከሚብረቀረቀው ጦርና አንካሴ ጋር፣የፍላጻው ኮረጆ ጐኑ ላይ ይንኳኳል።

24. በወኔ መሬቱን እየጐደፈረ ወደ ፊት ይሸመጥጣል፤የመለከት ድምፅ ሲሰማ ያቅበጠብጠዋል።

25. መለከቱ ሲያንባርቅ፣ ‘እሰይ’ ይላል፤የአዛዦችን ጩኸትና የሰራዊቱን ውካታ፣ጦርነትንም ከሩቅ ያሸታል።

26. “ጭልፊት የሚበረው፣ክንፎቹንም ወደ ደቡብ የሚዘረጋው፣ በአንተ ጥበብ ነውን?

27. ንስር ወደ ላይ የሚመጥቀው፣ጎጆውንም በከፍታ ላይ የሚሠራው፣በአንተ ትእዛዝ ነውን?

28. በገደል ላይ ይኖራል፤ በዚያም ያድራል፤ምሽጉም የቋጥኝ ጫፍ ነው።

29. እዚያ ሆኖ የሚነጥቀውን ይቃኛል፤ዐይኑም ከሩቅ አጥርቶ ያያል።

30. ጫጩቶቹ ደም ይጠጣሉ፤እርሱም በድን ካለበት አይታጣም።”