ምዕራፎች

  1. 1
  2. 2
  3. 3
  4. 4
  5. 5
  6. 6
  7. 7
  8. 8
  9. 9
  10. 10
  11. 11
  12. 12
  13. 13
  14. 14
  15. 15
  16. 16
  17. 17
  18. 18
  19. 19
  20. 20
  21. 21
  22. 22
  23. 23
  24. 24
  25. 25
  26. 26
  27. 27
  28. 28
  29. 29
  30. 30
  31. 31
  32. 32
  33. 33
  34. 34
  35. 35
  36. 36
  37. 37
  38. 38
  39. 39
  40. 40
  41. 41
  42. 42

ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ኢዮብ 28 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

1. “የብር ማዕድን የሚወጣበት፣ወርቅም የሚነጠርበት ስፍራ አለ።

2. ብረት ከመሬት ውስጥ ይገኛል፤መዳብም ከማዕድን ድንጋይ ቀልጦ ይወጣል።

3. ሰው፣ እስከ ጨለማ መጨረሻ ይዘልቃል፤ከድቅድቅ ጨለማ የማዕድን ድንጋይ ለማግኘት፣እስከ ውስጠኛው ዋሻ ገብቶ ይፈልጋል።

4. የሰው እግር ረግጦት በማያውቅበት ስፍራ፣ከሰዎች መኖሪያ ርቆ መውረጃ ጒድጓድ ይቈፍራል፤ሰው በሌለበት ቦታ ይንጠላጠላል፤ ይወዛወዛል።

5. ከላይዋ ምግብን የምታስገኝ ምድር፣ከታች በእሳት እንደሚሆን ትለዋወጣለች።

6. ሰንፔር ከዐለቷ ይወጣል፤ከዐፈሯም የወርቅ አንኳር ይገኛል።

7. ያን መንገድ ጭልፊት አያውቀውም፤የአሞራም ዐይን አላየውም፣

8. ኵሩ አራዊት አልረገጡትም፤አንበሳም በዚያ አላለፈም።

9. ሰው እጁን በቡላድ ድንጋይ ላይ ያነሣል፤ተራሮችንም ከሥር ይገለብጣል።

10. በድንጋይ ውስጥ መተላለፊያ ያበጃል፤ዐይኖቹም የከበሩ ነገሮችን ሁሉ ያያሉ።

11. የወንዞችን ምንጭ ይበረብራል፤የተሰወረውንም ነገር ወደ ብርሃን ያወጣል።

12. “ነገር ግን ጥበብ ከወዴት ትገኛለች?ማስተዋልስ መኖሪያዋ የት ነው?

13. ሰው ዋጋዋን አያውቅም፤በሕያዋንም ምድር አትገኝም።

14. ውቅያኖስ፣ ‘በእኔ ውስጥ የለችም’ ይላል፤ባሕርም፣ ‘በእኔ ዘንድ አይደለችም’ ይላል።

15. ንጹሕ ወርቅ ሊገዛት አይችልም፤ዋጋዋም በብር አይመዘንም።

16. በኦፊር ወርቅ፣በከበረም መረግድና በሰንፔር አትገመትም።

17. ወርቅም ብርሌም አይወዳደሯትም፤በወርቅ ጌጥም አትለወጥም።

18. ዛጐልና አልማዝ ከቍጥር አይገቡም፤የጥበብ ዋጋ ከቀይ ዕንቍም ይበልጣል።

19. የኢትዮጵያ ቶጳዝዮን ሊስተካከላት አይችልም፤ዋጋዋም በንጹሕ ወርቅ አይተመንም።

20. “ታዲያ፣ ጥበብ ከወዴት ትመጣለች?ማስተዋልስ የት ትገኛለች?

21. ከሕያዋን ፍጥረታት ዐይን ሁሉ ተሰውራለች፤ከሰማይ ወፎችም ተሸሽጋለች።

22. ጥፋትና ሞት፣‘ወሬዋን ብቻ ሰማን’ ይላሉ።

23. ወደ እርሷ የሚወስደውን መንገድ የሚረዳ፣መኖሪያዋንም የሚያውቅ እግዚአብሔር ብቻ ነው፤

24. እርሱ የምድርን ዳርቻ ይመለከታልና፤ከሰማይ በታች ያለውንም ሁሉ ያያል።

25. ለነፋስ ኀይልን በሰጠ ጊዜ፣የውሆችን መጠን በለካ ጊዜ፣

26. ለዝናብ ሥርዐትን፣ለነጐድጓድም መንገድን ባበጀ ጊዜ፣

27. በዚያን ጊዜ ጥበብን ተመለከታት፤ ገመገማትም፤አጸናት፤ መረመራትም።

28. ከዚያም ሰውን፣‘እግዚአብሔርን መፍራት ጥበብ ነው፤ከክፋትም መራቅ ማስተዋል ነው’ አለው።”