ምዕራፎች

  1. 1
  2. 2
  3. 3
  4. 4
  5. 5
  6. 6
  7. 7
  8. 8
  9. 9
  10. 10
  11. 11
  12. 12
  13. 13
  14. 14
  15. 15
  16. 16
  17. 17
  18. 18
  19. 19
  20. 20
  21. 21
  22. 22
  23. 23
  24. 24
  25. 25
  26. 26
  27. 27
  28. 28
  29. 29
  30. 30
  31. 31
  32. 32
  33. 33
  34. 34
  35. 35
  36. 36
  37. 37
  38. 38
  39. 39
  40. 40
  41. 41
  42. 42
  43. 43
  44. 44
  45. 45
  46. 46
  47. 47
  48. 48
  49. 49
  50. 50
  51. 51
  52. 52

ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ኤርምያስ 23 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

ጻድቁ ቅርንጫፍ

1. “በማሰማሪያ ቦታዬ ያሉትን በጎቼን ለሚያጠፉና ለሚበትኑ እረኞች ወዮላቸው!” ይላል እግዚአብሔር።

2. ስለዚህ የእስራኤል አምላክ እግዚአብሔር ሕዝቤን ስለሚጠብቁ እረኞች እንዲህ ይላል፤ “መንጋዬን ስለ በተናችሁ፣ ስላባረራችሁና ተገቢውን ጥንቃቄ ስላላደረጋችሁላቸው፣ ለክፋታችሁ ተገቢውን ቅጣት አመጣባችኋለሁ” ይላል እግዚአብሔር፤

3. “የመንጋዬንም ቅሬታ ካባረርሁባቸው አገሮች ሁሉ እኔ ራሴ ሰብስቤ፣ ወደ መሰማሪያቸው እመልሳቸዋለሁ፤ በዚያም ፍሬያማ ይሆናሉ፤ ይበዛሉም።

4. የሚጠብቋቸውን እረኞች አስነሣላቸዋለሁ፤ ከእንግዲህም አይፈሩም፤ አይደነግጡም ከእነርሱም አንድ እንኳ አይጐድልም” ይላል እግዚአብሔር።

5. “እነሆ፤ ለዳዊት፣ጻድቅ ቅርንጫፍ የማስነሣበት ጊዜ ይመጣል፤እርሱም ፍትሕንና ጽድቅን የሚያደርግ፣በጥበብ የሚገዛ ንጉሥ ይሆናል” ይላል እግዚአብሔር።

6. በእርሱም ዘመን ይሁዳ ይድናል፤እስራኤልም በሰላም ይኖራል፤የሚጠራበትም ስም፣‘እግዚአብሔር ጽድቃችን’ የሚል ነው።

7. “ስለዚህ ሰዎች፣ ‘እስራኤላውያንን ከግብፅ ምድር ያወጣ ሕያው እግዚአብሔርን!’ ብለው ከእንግዲህ የማይምሉበት ዘመን ይመጣል” ይላል እግዚአብሔር፤

8. ነገር ግን፣ ‘እስራኤልን ከሰሜን ምድርና እነርሱን ከበተነባቸው ከሌሎች አገሮች ያወጣ ሕያው እግዚአብሔርን’ ይላሉ፤ ከዚያ በኋላ በገዛ ምድራቸው ይኖራሉ።

ሐሰተኛ ነቢያት

9. ስለ ነቢያት፣ልቤ በውስጤ ተሰብሮአል፤ዐጥንቶቼም ተብረክርከዋል፤ ከእግዚአብሔር የተነሣ፣ከቅዱስ ቃሉም የተነሣ፣የወይን ጠጅ እንዳሸነፈው፣እንደ ሰካራም ሰው ሆኛለሁ።

10. ምድሪቱ በአመንዝሮች ተሞልታለች፤ከርግማን የተነሣ ምድሪቱ ታለቅሳለች፤በምድረ በዳ ያሉት መሰማሪያዎች ደርቀዋል።ነቢያቱም ጠማማ መንገድ ተከትለዋል፤ሥልጣናቸውን ያለ አግባብ ተጠቅመዋል።

11. “ነቢዩም፣ ካህኑም በጽድቅ መንገድ የማይሄዱ ናቸው፤በቤተ መቅደሴ እንኳ ሳይቀር ክፋታቸውን አይቻለሁ።”ይላል እግዚአብሔር።

12. “ስለዚህ መንገዳቸው ድጥ ይሆናል፤ወደ ጨለማ ይጣላሉ፤ተፍገምግመውም ይወድቃሉ፤በሚቀጡበትም ዓመት፣መዓት አመጣባቸዋለሁ፤”ይላል እግዚአብሔር።

13. “በሰማርያ ባሉ ነቢያት ላይ፣ደስ የማያሰኝ ነገር አይቻለሁ፤በበኣል ስም ትንቢት ተናገሩ፤ሕዝቤን እስራኤልን አሳቱ።

14. በኢየሩሳሌም ባሉ ነቢያትም ላይ፣የሚዘገንን ነገር አይቻለሁ፤ያመነዝራሉ፤ በመዋሸትም ይኖራሉ፤ማንም ከክፋቱ እንዳይመለስ፣የክፉዎችን እጅ ያበረታሉ፤በእኔ ዘንድ ሁሉም እንደ ሰዶም፣ነዋሪዎቿም እንደ ገሞራ ናቸው።”

15. ስለዚህ የሰራዊት ጌታ እግዚአብሔር ስለ እነዚህ ነቢያት እንዲህ ይላል፤“ከኢየሩሳሌም ነቢያት፣በምድሪቱ ሁሉ ርኵሰት ተሠራጭቶአልና፤መራራ ምግብ አበላቸዋለሁ፤የተመረዘም ውሃ አጠጣቸዋለሁ።”

16. የሰራዊት ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፤“እነዚህ ነቢያት የሚተነብዩላችሁን አትስሙ፤በባዶ ተስፋ ይሞሏችኋል፤ ከእግዚአብሔር አፍ የወጣ ሳይሆን፣ከገዛ ልባቸው የሆነውን ራእይ ይናገራሉ።

17. እኔን ለሚንቁኝ፣‘እግዚአብሔር ሰላም ይሆንላችኋል ብሏል’ ይላሉ፤የልባቸውን እልኸኝነት ለሚከተሉም ሁሉ፣‘ክፉ ነገር አይነካችሁም’ ይሏቸዋል።

18. ቃሉን ለማየትና ለመስማት፣እነማን የእግዚአብሔር ምክር ባለበት ቆመዋል?ቃሉን ያደመጠ፣ የሰማስ ማን ነው?

19. እነሆ፤ የእግዚአብሔር ዐውሎ ነፋስ፣በቍጣ ይነሣል፤ብርቱም ማዕበል፣የክፉዎችን ራስ ይመታል።

20. እግዚአብሔር የልቡን ሐሳብ፣ሙሉ በሙሉ ሳይፈጽም፣ቍጣው እንዲሁ አይመለስም፤በኋለኛው ዘመን፣ይህን በግልጽ ትረዳላችሁ።

21. እኔ እነዚህን ነቢያት አልላክኋቸውም፤እነርሱ ግን ለራሳቸው መልእክታቸውን ይዘው ሮጡ፣ሳልናገራቸውም፣ትንቢት ተናገሩ።

22. ምክሬ ባለበት ቢቆሙ ኖሮ፣ቃሌን ለሕዝቤ ባሰሙ ነበር፤ከክፉ መንገዳቸው፣ከክፉ ሥራቸውም በመለሷቸው ነበር።

23. “እኔ የቅርብ አምላክ ብቻ ነኝን?ይላል እግዚአብሔር፤“የሩቅስ አምላክ አይደለሁምን?

24. እኔ እንዳላየው፣በስውር ቦታ ሊሸሸግ የሚችል አለን?”ይላል እግዚአብሔር።“ሰማይንና ምድርንስ የሞላሁ እኔ አይደለሁምን”ይላል እግዚአብሔር።

25. “ ‘ሕልም አለምሁ ሕልም አለምሁ’ እያሉ በስሜ የሐሰት ትንቢት የሚናገሩትን የነቢያትን ቃል ሰምቻለሁ፤

26. ይህ ነገር፣ የገዛ ልባቸውን ሽንገላ በሚተነብዩ በሐሰተኞች ነቢያት ልብ ውስጥ የሚቈየው እስከ መቼ ነው?

27. አባቶቻቸው በኣልን በማምለክ ስሜን እንደ ረሱ፣ እነርሱ በሚነጋገሩት ሕልም፣ ሕዝቤ ስሜን እንዲረሳ ያደረጉ ይመስላቸዋል።

28. ሕልመኛ ነቢይ ሕልሙን ያውራ፤ ቃሌ ያለው ግን በታማኝነት ይናገር፤ ገለባና እህል ምን አንድ አድርጎአቸው!” ይላል እግዚአብሔር።

29. “ቃሌ እንደ እሳት፣ ድንጋይንም እንደሚያደቅ መዶሻ አይደለምን?” ይላል እግዚአብሔር።

30. “ስለዚህ ቃሌን እርስ በእርስ በመሰራረቅ ከእኔ እንደ ተቀበሉ አድርገው የሚናገሩትን ነቢያት እቃወማለሁ” ይላል እግዚአብሔር።

31. “አፈጮሌነታቸውን በመጠቀም፣ ‘እግዚአብሔር እንዲህ ይላል’ የሚሉትን ነቢያት እቃወማለሁ” ይላል እግዚአብሔር፤

32. “እነሆ፤ ሐሰተኛ ሕልም ተመርኵዘው ትንቢት የሚናገሩትን ነቢያት እቃወማለሁ” ይላል እግዚአብሔር፤ እኔ ሳልልካቸው ወይም ሳልሾማቸው ደፍረው ውሸት ይናገራሉ፤ ሕዝቤንም ያስታሉ፤ ለዚህም ሕዝብ አንዳች አይረቡትም” ይላል እግዚአብሔር።

የእግዚአብሔር ሸክም ምንድ ነው?

33. “ይህ ሕዝብ ወይም ነቢይ ወይም ካህን፣ ‘የእግዚአብሔር ሸክም ምንድን ነው?’ ብለው ቢጠይቁ፣ ‘ሸክሙ እናንተ ናችሁ፤ እወረውራችኋለሁ ይላል እግዚአብሔር’ ብለህ መልስላቸው።

34. ነቢይ ወይም ካህን ወይም ማንኛውም ሰው፣ ‘የእግዚአብሔር ሸክም’ እያለ ቢናገር፣ ያን ሰውና ቤቱን እቀጣለሁ።

35. እያንዳንዱ ለባልንጀራው ወይም ለዘመዱ፣ ‘እግዚአብሔር ምን መልስ ሰጠ?’ ወይም፣ ‘እግዚአብሔር ምን ተናገረ?’ ማለት ይገባዋል።

36. ከእንግዲህ ግን፣ ‘የእግዚአብሔር ሸክም’ ብላችሁ መናገር አይገባችሁም፤ ምክንያቱም ለሰው ሁሉ የገዛ ራሱ ቃል ሸክሙ ስለሚሆን፣ የአምላካችንን የሰራዊት ጌታ የእግዚአብሔርን፣ የሕያው አምላክን ቃል ታጣምማላችሁ።

37. ስለዚህ ለነቢዩ፣ ‘እግዚአብሔር ምን መልስ ሰጠህ’ ወይም፣ ‘እግዚአብሔር ምን ተናገረህ?’ ትለዋለህ፤

38. ‘የእግዚአብሔር ሸክም’ ብትሉ እንኳ፣ እግዚአብሔር ግን እንዲህ ይላል፤ ‘እኔ፣ “የእግዚአብሔር ሸክም” አትበሉ ብዬ ብነግራችሁም፣ እናንተ፣ “የእግዚአብሔር ሸክም” ብላችኋል፤

39. ስለዚህ እናንተን፣ እንዲሁም ለእናንተና ለአባቶቻችሁ የሰጠኋትን ከተማ ጭምር ፈጽሜ እተዋችኋለሁ፤ ከፊቴ እጥላችኋለሁ፤

40. ለዘላለም የማይረሳ ዕፍረት፣ የዘላለምም ውርደት አመጣባችኋለሁ።