ምዕራፎች

  1. 1
  2. 2
  3. 3
  4. 4
  5. 5
  6. 6
  7. 7
  8. 8
  9. 9
  10. 10
  11. 11
  12. 12
  13. 13
  14. 14
  15. 15
  16. 16
  17. 17
  18. 18
  19. 19
  20. 20
  21. 21
  22. 22
  23. 23
  24. 24
  25. 25
  26. 26
  27. 27
  28. 28
  29. 29
  30. 30
  31. 31
  32. 32
  33. 33
  34. 34
  35. 35
  36. 36
  37. 37
  38. 38
  39. 39
  40. 40
  41. 41
  42. 42
  43. 43
  44. 44
  45. 45
  46. 46
  47. 47
  48. 48
  49. 49
  50. 50
  51. 51
  52. 52

ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ኤርምያስ 49 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

ስለ አሞን የተነገረ መልእክት

1. ስለ አሞናውያን፤ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፤“እስራኤል ወንዶች ልጆች አልወለደምን?ወራሾችስ የሉትምን?ታዲያ፣ ሚልኮምሸ ጋድን ለምን ወረሰ?የእርሱ ሰዎች ለምን በከተሞቿ ይኖራሉ?

2. ስለዚህ በአሞናውያን ከተማ በረባት ላይ፣የጦርነት ውካታ ድምፅ፣የሚሰማበት ጊዜ ይመጣል፤”ይላል እግዚአብሔር፤“እርሷም የፍርስራሽ ክምር ትሆናለች፤በዙሪያዋ ያሉት መንደሮችም ይቃጠላሉ፤እስራኤልም ከአገሯ ያስወጧትን፣ከአገሯ ታስወጣለች፤”ይላል እግዚአብሔር፤

3. ሐሴቦን ሆይ፤ ጋይ ጠፍታለችና ዋይ በይ፤የራባት ሴቶች ልጆች ሆይ ጩኹ፤ማቅ ለብሳችሁ አልቅሱ፤ሚልኮም ከካህናቱና ከመኳንንቱ ጋር፣ተማርኮ ይወሰዳልና፣በቅጥር ውስጥ ወዲያ ወዲህ ተሯሯጡ።

4. አንቺ ከዳተኛ ልጅ ሆይ፣በሸለቆችሽ ለምን ትመኪያለሽ?ለምንስ በፍሬያማ ሸለቆሽ ትኵራሪያለሽ?በብልጽግናሽ ተማምነሽ፣‘ማን ሊነካኝ ይችላል?’ ትያለሽ።

5. በዙሪያሽ ካሉት ሁሉ ዘንድ፣ሽብር አመጣብሻለሁ፤”ይላል የሰራዊት ጌታ እግዚአብሔር፤“እያንዳንዳችሁ ትሰደዳላችሁ፤በሽሽት ላይ ያሉትንም የሚሰበስብ አይገኝም።

6. “ከዚያ በኋላ ግን፣ የአሞናውያንን ምርኮ እመልሳለሁ፣”ይላል እግዚአብሔር።

ስለ ኤዶም የተነገረ መልእክት

7. ስለ ኤዶም፤የሰራዊት ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፤“ጥበብ ከቴማን ጠፍቶአልን?ምክር ከአስተዋዮች ርቆአልን?ጥበባቸውስ ተሟጧልን?

8. ዔሳውን በምቀጣ ጊዜ፣ጥፋት ስለማመጣበት፣እናንተ በድዳን የምትኖሩ ሆይ፤ወደ ኋላ ተመልሳችሁ ሽሹ፤ ጥልቅ ጒድጓድ ውስጥ ተደበቁ።

9. ወይን ለቃሚዎች ወዳንተ ቢመጡ፣ጥቂት ወይን አያስቀሩምን?ሌቦችስ በሌሊት ቢመጡ፣የሚሰርቁት የሚፈልጉትን ብቻ አይደለምን?

10. እኔ ግን ዔሳውን አራቍተዋለሁ፤መደበቅም እንዳይችል፣መሸሸጊያ ስፍራዎቹን እገልጣለሁ፤ልጆቹ፣ ዘመዶቹና ጎረቤቶቹ ይጠፋሉ፤እርሱም ራሱ አይኖርም።

11. ወላጆች የሌላቸውን ልጆችህን ተዋቸው፤ እኔ ለሕይወታቸው እጠነቀቃለሁ፤ መበለቶቻችሁም በእኔ ይታመኑ።”

12. እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፤ “ከጽዋው መጠጣት የማይገባቸው ሊጠጡ ግድ ከሆነ፣ አንተ እንዴት ሳትቀጣ ትቀራለህ? መቀጣትህ አይቀርም፤ መጠጣት ይገባሃል።

13. ባሶራ ፈራርሳ የድንጋጤ፣ የመዘባበቻና የርግማን ምልክት እንደምትሆን በራሴ ምያለሁ” ይላል እግዚአብሔር፤ “ከተሞቿም ሁሉ ለዘላለም ባድማ ይሆናሉ።”

14. ከእግዚአብሔር ዘንድ መልእክት ሰምቻለሁ፤“እርሷን ለመውጋት ተሰብሰቡ፤ለጦርነትም ውጡ”የሚል መልእክተኛ ወደ ሕዝቦች ተልኮአል።

15. “እነሆ፤ በሕዝቦች መካከል ታናሽ፣በሰዎችም ዘንድ የተናቅህ አደርግሃለሁ።

16. አንተ በዐለት ንቃቃት ውስጥ የምትኖር፣የተራራውንም ከፍታ የያዝህ ሆይ፤የምትነዛው ሽብር፣የልብህም ኵራት አታሎሃል፤መኖሪያህን እንደ ንስር በከፍታ ቦታ ብትሠራም፣ከዚያ ወደ ታች እጥልሃለሁ፤”ይላል እግዚአብሔር።

17. “ኤዶም የድንጋጤ ምልክት ትሆናለች፤ከቍስሎቿም ሁሉ የተነሣ፣በዚያ የሚያልፍ ሁሉ በመደነቅ ያላግጥባታል።”

18. በዙሪያቸው ካሉት ከተሞች ጋር፣ሰዶምና ገሞራ እንደ ተገለበጡ፣”ይላል እግዚአብሔር፤እንዲሁ ማንም በዚያ አይኖርም፤አንድም ሰው አይቀመጥባትም።

19. “አንበሳ ከዮርዳኖስ ደኖች፣ወደ ግጦሽ ሜዳ ብቅ እንደሚል፣እኔም በኤዶም ላይ ድንገት እወጣለሁ፤ ከምድሩም አባርረዋለሁ።የመረጥሁትን በእርሱ ላይ እሾማለሁ፤እንደ እኔ ያለ ማን ነው? ማንስ ሊገዳደረኝ ይችላል?የትኛውስ እረኛ ሊቋቋመኝ ይችላል?

20. ስለዚህ እግዚአብሔር በኤዶም ላይ ያለውን ዕቅድ፣በቴማን በሚኖሩትም ላይ ያሰበውን አሳብ ስሙ፤ታናናሹ መንጋ ተጐትቶ ይወሰዳል፤በእነርሱም ምክንያት መሰማሪያቸውን ፈጽሞ ያጠፋል።

21. በውድቀታቸው ድምፅ ምድር ትናወጣለች፤ጩኸታቸውም እስከ ቀይ ባሕር ያስተጋባል።

22. እነሆ፤ እንደ ንስር ተወርውሮ ይወርድባታል፤ክንፎቹንም በባሶራ ላይ ይዘረጋል፤በዚያን ቀን የኤዶም ጦረኞች ልብ፣በምጥ እንደ ተያዘች ሴት ልብ ይሆናል።

ስለ ደማስቆ የተነገረ መልእክት

23. ስለ ደማስቆ፤“ክፉ ወሬ ሰምተዋልና፣ሐማትና አርፋድ ደንግጠዋል፤እንደ ተናወጠ ባሕርም ታውከዋል፤ልባቸውም ቀልጦአል።

24. ደማስቆ ተዳከመች፤ትሸሽም ዘንድ ወደ ኋላ ተመለሰች፤ብርክ ያዛት፣ምጥ እንደ ያዛት ሴት፣ጭንቅና መከራ ዋጣት።

25. ደስ የምሰኝባት፣የታወቀችው ከተማ እንዴት ተተወች?

26. በርግጥ ወንዶች ወጣቶቿ በየአደባባዩ ይረግፋሉ፤በዚያ ቀን ወታደሮቿ ሁሉ ይወድቃሉ፤”ይላል የሰራዊት ጌታ እግዚአብሔር፤

27. “በደማስቆ ቅጥር ላይ እሳት እለኵሳለሁ፤የወልደ አዴርንም ዐምባ ይበላል።”

ስለ ቄዳርና ስለ ሐጾር የተነገረ መልእክት

28. የባቢሎን ንጉሥ ናቡከደነፆር ስለ ወጋቸው ስለ ቄዳርና ስለ ሐጾር መንግሥታት የተነገረ፤ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፤“ተነሡ፣ ቄዳርን ውጉ፤የምሥራቅንም ሕዝብ ደምስሱ።

29. ድንኳኖቻቸውና መንጎቻቸው ይወሰዳሉ፤መጠለያቸውና ግመሎቻቸው ሳይቀሩ፣ከነዕቃዎቸው ይነጠቃሉ፤ሰዎች፣ ‘ሽብር በሽብር ላይ መጥቶባቸዋል፤’እያሉ ይጮኹባቸዋል።

30. በሐጾር የምትኖሩ ሆይ፣በጥድፊያ ሽሹ በጥልቅ ጒድጓድ ተሸሸጉ፤”ይላል እግዚአብሔር፤የባቢሎን ንጉሥ ናቡከደነፆር በእናንተ ላይ መክሮአልና፣ወረራም ዶልቶባችኋል።

31. “ተነሡ፣ ተዘልሎ የተቀመጠውን፣በራሱ ተማምኖ የሚኖረውን ሕዝብ ውጉ፤”ይላል እግዚአብሔር፤“መዝጊያና መቀርቀሪያ በሌለው፤ለብቻው በሚኖረው ሕዝብ ላይ ዝመቱ።

32. ግመሎቻቸው ይዘረፋሉ፤ከብቶቻቸውንም አንጋግተው ይነዱባቸዋል፤ጠጒሩን የሚቀነብበውን ወገንእበትናለሁ ከየአቅጣጫው መዓትይላል እግዚአብሔር፤

33. “ሐጾር የቀበሮዎች መፈንጫ፣ለዘላለም ባድማ ትሆናለች፤ማንም በዚያ አይኖርም፤የሚቀመጥባትም አይገኝም።”

ስለ ኤላም የተነገረ መልእክት

34. በይሁዳ ንጉሥ በሴዴቅያስ ዘመነ መንግሥት መጀመሪያ ላይ ወደ ነቢዩ ወደ ኤርምያስ የመጣው የእግዚአብሔር ቃል ይህ ነው፤

35. የሰራዊት ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፤“እነሆ፤ የኀያልነቷን መሠረት፣የኤላምን ቀስት እሰብራለሁ።

36. ከአራቱ የሰማይ ማእዘናት፣በኤላም ላይ አራቱን ነፋሳት አመጣለሁ፤ወደ አራቱም ነፋሳት እበትናቸዋለሁ፤ከኤላም የሚማረኩት የማይደርሱበት፣አገር አይገኝም።

37. ነፍሳቸውን በሚሹ ጠላቶቻቸው ፊት፣ኤላምን አርበደብዳለሁ፤በላያቸው ላይ መዓትን፣ይኸውም ቍጣዬን አመጣባቸዋለሁ፤”ይላል እግዚአብሔር፤“ፈጽሜ አስካጠፋቸውም ድረስ፣በሰይፍ አሳድዳቸዋለሁ።

38. ዙፋኔን በኤላም እዘረጋለሁ፤ነገሥታቷንና መኳንንቷን አጠፋለሁ፤”ይላል እግዚአብሔር፤

39. “ነገር ግን የኋላ ኋላ፣የኤላምን ምርኮ እመልሳለሁ፤”ይላል እግዚአብሔር።