ምዕራፎች

  1. 1
  2. 2
  3. 3
  4. 4
  5. 5
  6. 6
  7. 7
  8. 8
  9. 9
  10. 10
  11. 11
  12. 12
  13. 13
  14. 14
  15. 15
  16. 16
  17. 17
  18. 18
  19. 19
  20. 20
  21. 21
  22. 22
  23. 23
  24. 24
  25. 25
  26. 26
  27. 27
  28. 28
  29. 29
  30. 30
  31. 31
  32. 32
  33. 33
  34. 34
  35. 35
  36. 36
  37. 37
  38. 38
  39. 39
  40. 40
  41. 41
  42. 42
  43. 43
  44. 44
  45. 45
  46. 46
  47. 47
  48. 48
  49. 49
  50. 50
  51. 51
  52. 52

ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ኤርምያስ 31 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

1. “በዚያ ዘመን” ይላል እግዚአብሔር፤ “ለእስራኤል ነገድ ሁሉ አምላካቸው እሆናለሁ፤ እነርሱም ሕዝቤ ይሆናሉ።”

2. እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፤“ከሰይፍ የተረፈው ሕዝብ፣በምድረ በዳ ሞገስን ያገኛል፤እኔም ለእስራኤል ዕረፍት ለመስጠት እመጣለሁ።”

3. እግዚአብሔር ከሩቅ ተገለጠልን፤ እንዲህም አለን፤“በዘላለማዊ ፍቅር ወድጄሻለሁ፤ስለዚህም በርኅራኄ ሳብሁሽ።

4. የእስራኤል ድንግል ሆይ፤ እንደ ገና አንጽሻለሁ፤አንቺም ትታነጪያለሽ፤ከበሮችሽንም እንደ ገና አንሥተሽ፣ከሚፈነጥዙት ጋር ትፈነድቂያለሽ።

5. እንደ ገናም በሰማርያ ኰረብቶች ላይ፣ወይን ትተክያለሽ፤አትክልተኞች ይተክሏቸዋል፤በፍሬውም ደስ ይላቸዋል።

6. ጠባቂዎች፣ በኤፍሬም ኰረብቶች ላይ፣‘ኑ፤ ወደ ጽዮን፣ወደ አምላካችን ወደ እግዚአብሔር እንውጣ!’ብለው የሚጮኹበት ቀን ይመጣል።

7. እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፤“ስለ ያዕቆብ በደስታ ዘምሩ፤ስለ ሕዝቦች አለቃ እልል በሉ፤ምስጋናችሁን አሰሙ፤‘እግዚአብሔር ሆይ፤ የእስራኤልን ቅሬታ፣ሕዝብህን አድን’ በሉ።

8. እነሆ፤ ከሰሜን ምድር አመጣቸዋለሁ፤ከምድርም ዳርቻ እሰበስባቸዋለሁ፤በመካከላቸውም ዕውሮችና አንካሶች፣ነፍሰ ጡርና በምጥ ላይ ያሉ ሴቶች ይገኛሉ፤ታላቅም ሕዝብ ሆነው ይመለሳሉ።

9. እያለቀሱ ይመጣሉ፤እያጽናናሁ አመጣቸዋለሁ፤እኔ ለእስራኤል አባት ነኝና፣ኤፍሬም በኵር ልጄ ነውና፣በውሃ ምንጭ ዳር፣በማይሰናከሉበት ቀና መንገድ እመራቸዋለሁ።

10. “ሕዝቦች ሆይ፤ የእግዚአብሔርን ቃል ስሙ፤ሩቅ ባሉ የባሕር ጠረፎችም፣‘እስራኤልን የበተነ እርሱ ይሰበስበዋል፤መንጋውንም እንደ እረኛ ይጠብቃል’ ብላችሁ ዐውጁ።

11. እግዚአብሔር ያዕቆብን ይዋጀዋልና፤ከእርሱም ከሚበረቱት እጅ ይታደገዋልና።

12. መጥተውም በጽዮን ተራራ ላይ በደስታ ይዘምራሉ፤ በእግዚአብሔርም ልግስና፣በእህሉ፣ በወይን ጭማቂውና በዘይቱ፣በፍየልና በበግ ጠቦት፣ በወይፈንና በጊደር ደስ ይሰኛሉ፤ውሃ እንደማይቋረጥባት የአትክልት ስፍራ ይሆናሉ፤ከእንግዲህም አያዝኑም።

13. ኰረዶች ይዘፍናሉ፤ ደስም ይላቸዋል፤ጐረምሶችና ሽማግሌዎችም ይፈነጥዛሉ፤ልቅሶአቸውን ወደ ደስታ እለውጣለሁ፤ከሐዘናቸውም አጽናናቸዋለሁ፤ ደስታንም እሰጣቸዋለሁ።

14. ካህናቱን አትረፍርፌ እባርካለሁ፤ሕዝቤም በልግስናዬ ይጠግባል፤”ይላል እግዚአብሔር።

15. እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፤“ዋይታና መራራ ልቅሶ፣ከራማ ተሰማ፤ልጆቿ የሉምና፣ራሔል አለቀሰች፤መጽናናትም እንቢ አለች።”

16. እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፤“ድምፅሽን ከልቅሶ፣ዐይኖችሽንም ከእንባ ከልክይ፤ድካምሽ ያለ ዋጋ አይቀርምና፤”ይላል እግዚአብሔር።“ከጠላት ምድር ይመለሳሉ፤

17. ስለዚህ ወደ ፊት ተስፋ አለሽ”ይላል እግዚአብሔር።“ልጆችሽ ወደ ገዛ ምድራቸው ይመለሳሉ።

18. “የኤፍሬምን የሲቃ እንጒርጒሮ በእርግጥ ሰምቻለሁ፤‘እንዳልተገራ ወይፈን ቀጣኸኝ፤እኔም ተቀጣሁ።አንተ እግዚአብሔር አምላኬ ነህና፣መልሰኝ፤ እኔም እመለሳለሁ።

19. ከአንተ ከራቅሁ በኋላ፣ተመልሼ ተጸጸትሁ፤ባስተዋልሁም ጊዜ፣ጭኔን መታሁ፣የወጣትነት ውርደቴን ተሸክሜአለሁና፣ዐፈርሁ፤ ቀለልሁም።’

20. ኤፍሬም የምወደው፣ደስም የምሰኝበት ልጄ አይደለምን?ብዙ ጊዜ ተቃውሜው ብናገርም፣መልሼ ስለ እርሱ አስባለሁ፤አንጀቴ ይላወሳል፤በታላቅ ርኅራኄም እራራለታለሁ፤”ይላል እግዚአብሔር።

21. “የጐዳና ምልክት አቁሚ፤መንገድ አመልካች ትከዪ፤የምትሄጂበትን መንገድ፣አውራ ጐዳናውን አስተውዪ፤ድንግሊቱ እስራኤል ሆይ፤ ተመለሺ፤ወደ ከተሞችሽም ግቢ።

22. አንቺ ከዳተኛ ልጅ ሆይ፤እስከ መቼ ትቅበዘበዣለሽ? እግዚአብሔር በምድር ላይ አዲስ ነገር ይፈጥራል፤ሴት በወንድ ላይ ከበባ ታደርጋለች።

23. የእስራኤል አምላክ የሰራዊት ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፤ “ምርኮአቸውን በመለስሁላቸው ጊዜ፣ እነርሱ በይሁዳ ምድርና በከተሞቿ፣ ‘አንተ የጽድቅ ማደሪያ ቅዱስ ተራራ ሆይ፤ እግዚአብሔር ይባርክህ!’ የሚል አነጋገር እንደ ገና ይጠቀማሉ።

24. ገበሬዎችና ዘላን ከብት አርቢዎች በይሁዳና በከተሞቿ በአንድነት ይኖራሉ።

25. የዛለችውን ነፍስ ዐድሳለሁ፤ የደከመችውንም አበረታለሁ።”

26. በዚህ ጊዜ ከእንቅልፌ ነቅቼ ዙሪያዬን ተመለከትሁ፤ እንቅልፌም ጣፋጭ ሆኖልኝ ነበር።

27. “እነሆ፤ የእስራኤልን ቤትና የይሁዳን ቤት” ይላል እግዚአብሔር፤ “በሰውና በእንስሳት ዘር የምሞላበት ጊዜ ይመጣል፤

28. ልነቅላቸውና ላፈርሳቸው፣ ልገለብጣቸውና ላጠፋቸው፣ መከራም ላመጣባቸው እንደ ተጋሁ ሁሉ፣ ላንጻቸውና ልተክላቸው ደግሞ እተጋለሁ” ይላል እግዚአብሔር።

29. “በዚያ ዘመን ሰዎች ዳግመኛ፣‘አባቶች በበሉት ጐምዛዛ የወይን ፍሬ፣የልጆች ጥርስ ጠረሰ’ የሚለውን ምሳሌ አይናገሩም።

30. ነገር ግን፣ እያንዳንዱ በገዛ ኀጢአቱ ይሞታል፤ ጐምዛዛ የወይን ፍሬ የሚበላ ሁሉ የራሱን ጥርስ ይጠርሳል።

31. “ከእስራኤል ቤትና፣ከይሁዳ ቤት ጋር” ይላል እግዚአብሔር፤“አዲስ ቃል ኪዳን የምገባበት፣ጊዜ ይመጣል።

32. ከግብፅ አወጣቸው ዘንድ፣እጃቸውን ይዤ በመራኋቸው ጊዜ፣ከአባቶቻቸው ጋር እንደ ገባሁት ኪዳንአይደለም፤የእነርሱ ባልገ ሆኜ ሳለሁ፣ቃል ኪዳኔን አፍርሰዋልና።”ይላል እግዚአብሔር።

33. “ነገር ግን ከዚያ ጊዜ በኋላ፣ከእስራኤል ቤት ጋር የምገባው ኪዳን ይህ ነው” ይላል እግዚአብሔር፤“ሕጌን በልቡናቸው አኖራለሁ፤በልባቸውም እጽፈዋለሁ።እኔ አምላክ እሆናቸዋለሁ፤እነርሱም ሕዝቤ ይሆናሉ።

34. ከእንግዲህ ማንም ሰው ባልንጀራውን፣ወይም ወንድሙን፣ ‘እግዚአብሔርን ዕወቅ’ ብሎ አያስተምርም፤ከትንሹ ጀምሮ እስከ ትልቁ፣ሁሉም እኔን ያውቁኛልና፤”ይላል እግዚአብሔር።“በደላቸውን ይቅር እላለሁ፤ኀጢአታቸውንም መልሼ አላስብም።”

35. በቀን እንድታበራ፣ፀሓይን የመደበ፣በሌሊት እንዲያበሩ፣ጨረቃንና ከዋክብትን ያዘዛቸው፣የሞገዱ ድምፅ እንዲተምም፣ባሕሩን የሚያናውጥ፣ስሙ የሰራዊት ጌታ የሆነ፣ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፤

36. “ይህ ሥርዐት በፊቴ ከተሻረ፣”ይላል እግዚአብሔር፤“በዚያ ጊዜ የእስራኤልም ዘር በፊቴ፣መንግሥት መሆኑ ለዘላለም ይቀራል።”

37. እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፤“በላይ ያሉትን ሰማያትን መለካት፣በታችም ያሉትን የምድር መሠረቶች መመርመር ከተቻለ፣በዚያ ጊዜ የእስራኤልን ዘር ሁሉ፣ስላደረጉት ነገር ሁሉ እጥላቸዋለሁ፤”ይላል እግዚአብሔር።

38. “እነሆ ከሐናንኤል ግንብ ጀምሮ እስከ ማእዘኑ በር ድረስ” ይላል እግዚአብሔር፤ “ይህች ከተማ ለእግዚአብሔር የምትሠራበት ጊዜ ይመጣል፤

39. መለኪያ ገመዱም ከዚያ ጀምሮ በቀጥታ ወደ ጋሬብ ኰረብታ፣ አልፎም ወደ ጎዓ ይዘረጋል።

40. ሬሳና ዐመድ የሚጣልበት ሸለቆ በሙሉ፣ በምሥራቅ በኩል የቄድሮንን ሸለቆ ይዞ እስከ ፈረስ በር የሚደርሰው ደልዳላ ቦታ ሁሉ ለእግዚአብሔር የተቀደሰ ይሆናል፤ ከእንግዲህም ከተማይቱ አትነቀልም፤ አትፈርስምም።”