ምዕራፎች

  1. 1
  2. 2
  3. 3
  4. 4
  5. 5
  6. 6
  7. 7
  8. 8
  9. 9
  10. 10
  11. 11
  12. 12
  13. 13
  14. 14
  15. 15
  16. 16
  17. 17
  18. 18
  19. 19
  20. 20
  21. 21
  22. 22
  23. 23
  24. 24
  25. 25
  26. 26
  27. 27
  28. 28
  29. 29
  30. 30
  31. 31
  32. 32
  33. 33
  34. 34
  35. 35
  36. 36
  37. 37
  38. 38
  39. 39
  40. 40
  41. 41
  42. 42
  43. 43
  44. 44
  45. 45
  46. 46
  47. 47
  48. 48
  49. 49
  50. 50
  51. 51
  52. 52

ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ኤርምያስ 10 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

ባዕድ አምልኮና እውነተኛው አምልኮ

1. የእስራኤል ቤት ሆይ፤ እግዚአብሔር የሚላችሁን ስሙ።

2. እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፤“የአሕዛብን መንገድ አትከተሉ፤እነርሱ በሰማይ ምልክቶች ይታወካሉ፣እናንተ ግን በእነዚህ አትረበሹ።

3. የአሕዛብ ልማድ ከንቱ ነውና፤ዛፍ ከጫካ ይቈርጣሉ፤አናጺም በመሣሪያው ቅርጽ ያበጅለታል፤

4. በብርና በወርቅ ይለብጡታል፤እንዳይወድቅም፣በመዶሻ መትተው በምስማር ያጣብቁታል።

5. ጣዖቶቻቸው በዱባ ዕርሻ መካከል እንደ ቆመ ማስፈራርቾ ናቸው፤የመናገር ችሎታ የላቸውም፤መራመድም ስለማይችሉ፣ተሸካሚ ያስፈልጋቸዋል፤ጒዳት ማድረስም ሆነ፣መልካምን ነገር ማድረግ ስለማይችሉ፣አትፍሯቸው።”

6. እግዚአብሔር ሆይ፤ እንዳንተ ያለ ማንም የለም፤አንተ ታላቅ ነህ፤የስምህም ሥልጣን ታላቅ ነው።

7. የሕዝቦች ሁሉ ንጉሥ ሆይ፤አንተን የማይፈራ ማነው?ክብር ይገባሃልና።ከምድር ጠቢባን ሁሉ፣ከመንግሥቶቻቸውም ሁሉ መካከል፣እንዳንተ ያለ የለም።

8. ከከንቱ የዕንጨት ጣዖት ትምህርት የሚቀስሙ ሁሉ፣ጅሎችና ሞኞች ናቸው።

9. የተጠፈጠፈ ብር ከተርሴስ፣ወርቅም ከአፌዝ ይመጣል።ባለሙያውና አንጥረኛው የሠሯቸው፣ብልኀተኞችም ያበጇቸው ሁሉ፣ሰማያዊና ሐምራዊ ልብስ ተጐናጽፈዋል።

10. እግዚአብሔር ግን እውነተኛ አምላክ ነው፤እርሱ ሕያው አምላክ፣ ዘላለማዊም ንጉሥ ነው፤በሚቈጣበት ጊዜ ምድር ትንቀጠቀጣለች፤መንግሥታትም ቍጣውን ሊቋቋሙ አይችሉም።

11. “እናንተም፣ ‘እነዚህ ሰማያትንና ምድርን ያልፈጠሩ አማልክት ከምድር ላይ፣ ከሰማያትም በታች ይጠፋሉ’ ትሏቸዋላችሁ።”

12. እግዚአብሔር ግን ምድርን በኀይሉ ፈጠረ፤ዓለምን በጥበቡ መሠረተ፤ሰማያትንም በማስተዋሉ ዘረጋ።

13. ድምፁን ሲያንጐደጒድ፣ በሰማያት ያሉ ውሆች ይናወጣሉ፤ጉሙን ከምድር ዳር ወደ ላይ እንዲወጣ ያደርገዋል፤መብረቅን ከዝናብ ጋር ይልካል፤ነፋስንም ከግምጃ ቤቱ ያወጣል።

14. እያንዳንዳቸው ጅሎችና ዕውቀት የለሾች ናቸው።ወርቅ አንጥረኛውም ሁሉ በሠራው ጣዖት ዐፍሮአል፤የቀረጻቸው ምስሎቹ የሐሰት ናቸው፤እስትንፋስም የላቸውም።

15. እነርሱ ከንቱ የፌዝ ዕቃዎች ናቸው፤ፍርድ ሲመጣባቸው ይጠፋሉ።

16. የያዕቆብ ዕድል ፈንታ የሆነው ግን እንደነዚህ አይደለም፤እርሱ የሁሉ ነገር ፈጣሪ ነውና፤እስራኤልም የርስቱ ነገድ ነው።ስሙ የሰራዊት ጌታ እግዚአብሔር ነው።

ሊመጣ ያለው ግዞት

17. አንቺ የተከበብሽ፤ከያለበት ንብረትሽን ሰብስቢ፤

18. እግዚአብሔር እንዲህ ይላልና፤“በዚህች ምድር የሚኖሩትን፣አሁን ወደ ውጪ እወነጭፋቸዋለሁ፤ጒዳቱ እንዲሰማቸው፣መከራ አመጣባቸዋለሁ፤”

19. ስለ ስብራቴ ወዮልኝ፤ቍስሌም የማይድን ነው፤ግን ለራሴ እንዲህ አልሁት፤“ይህ የኔው ሕመም ነው ልሸከመውም ይገባኛል።”

20. ድንኳኔ ፈርሶአል፤ገመዶቹም ሁሉ ተበጣጥሰዋል፤ልጆቼ ጥለውኝ ሄደዋል፤ ከእንግዲህም አይመለሱም፤ድንኳኔን ለመትከል፣መጋረጃዬንም ለመዘርጋት ማንም የቀረ የለም።

21. እረኞቹ አእምሮ የላቸውም፤ እግዚአብሔርን አይጠይቁም፤ስለዚህ አልተከናወነላቸውም፤መንጎቻቸውም ሁሉ ተበታትነዋል።

22. መርዶ ስሙ! እነሆ፤ ከሰሜን ምድር፣ታላቅ ሽብር እየመጣ ነው፤የይሁዳን ከተሞች ባድማ፣የቀበሮዎችም መናኸሪያ ያደርጋል።

የኤርምያስ ጸሎት

23. እግዚአብሔር ሆይ፤ የሰው ሕይወት በራሱ እጅ እንዳልሆነች፣አካሄዱንም በራሱ አቃንቶ ሊመራእንደማይችል ዐውቃለሁ።

24. እግዚአብሔር ሆይ፤ ቅጣኝ፤ ብቻ በመጠኑ ይሁንልኝ፤ፈጽሞ እንዳልጠፋ፣በቍጣህ አትምጣብኝ።

25. ያዕቆብን አሟጠው ስለበሉት፣ፈጽመው ስለዋጡት፣መኖሪያውንም ወና ስላደረጉ፣በማያውቁህ ሕዝቦች፣ስምህንም በማይጠሩ ወገኖች ላይ፣ቍጣህን አፍስስ።