ምዕራፎች

  1. 1
  2. 2
  3. 3
  4. 4
  5. 5
  6. 6
  7. 7
  8. 8
  9. 9
  10. 10
  11. 11
  12. 12
  13. 13
  14. 14
  15. 15
  16. 16
  17. 17
  18. 18
  19. 19
  20. 20
  21. 21
  22. 22
  23. 23
  24. 24
  25. 25
  26. 26
  27. 27
  28. 28
  29. 29
  30. 30
  31. 31

ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ምሳሌ 14 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

1. ጠቢብ ሴት ቤቷን ትሠራለች፤ተላላ ሴት ግን በገዛ እጇ ታፈርሰዋለች።

2. አካሄዱ ቅን የሆነ ሰው እግዚአብሔርን ይፈራል፤መንገዱ ጠማማ የሆነ ግን ይንቀዋል።

3. የተላላ ሰው ንግግር ለጀርባው በትር ታስከትልበታለች፤የጥበበኛ ከንፈር ግን ትጠብቃቸዋለች።

4. በሬዎች በሌሉበት ገንዳው ባዶ ይሆናል፤በበሬ ጒልበት ግን ብዙ ምርት ይገኛል።

5. ታማኝ ምስክር አይዋሽም፤ሐሰተኛ ምስክር ግን ውሸትን ይዘከዝካል።

6. ፌዘኛ ጥበብን ይሻል፤ ሆኖም አያገኛትም፤ዕውቀት ግን ለአስተዋዮች በቀላሉ ትገኛለች።

7. ከተላላ ሰው ራቅ፤ከከንፈሮቹ ዕውቀት አታገኝምና።

8. የአስተዋዮች ጥበብ መንገዳቸውን ልብ ማለት ነው፤የተላሎች ሞኝነት ግን መታለል ነው።

9. ተላሎች በሚያቀርቡት የበደል ካሳ ያፌዛሉ፤በቅኖች መካከል ግን በጎ ፈቃድ ትገኛለች።

10. እያንዳንዱ ልብ የራሱን መራራ ሐዘን ያውቃል፤ደስታውንም ማንም ሊጋራው አይችልም።

11. የክፉዎች ቤት ይፈርሳል፤የቅኖች ድንኳን ግን ይስፋፋል።

12. ለሰው ቀና መስሎ የሚታይ መንገድ አለ፤በመጨረሻ ግን ወደ ሞት ያደርሳል።

13. በሣቅ ጊዜ እንኳ ልብ ይተክዛል፤ደስታም በሐዘን ሊፈጸም ይችላል።

14. ልባቸውን ከጽድቅ የሚመልሱ የእጃቸውን ሙሉ ዋጋ ይቀበላሉ፤ደግ ሰውም ወሮታውን ያገኛል።

15. ተላላ ሰው ሁሉን ያምናል፤አስተዋይ ግን ርምጃውን ያስተውላል።

16. ጠቢብ ሰው ጥንቁቅ ነው፤ ከክፉም ይርቃል፤ተላላ ግን ችኵልና ደንታ ቢስ ነው።

17. ግልፍተኛ ሰው የቂል ተግባር ይፈጽማል፤መሠሪም ሰው አይወደድም።

18. ብስለት የሌላቸው ተላላነትን ይወርሳሉ፤አስተዋዮች ግን ዕውቀትን እንደ ዘውድ ይጭናሉ።

19. ክፉዎች በደጎች ፊት፣ኀጥኣንም በጻድቃን ደጅ ያጐነብሳሉ።

20. ድኾችን ወዳጆቻቸው እንኳ ይጠሏቸዋል፤ባለጠጎች ግን ብዙ ወዳጆች አሏቸው።

21. ጎረቤቱን የሚንቅ ኀጢአት ይሠራል፤ለተቸገሩት የሚራራ ግን ቡሩክ ነው።

22. ክፉ ነገር የሚያቅዱ ከትክክለኛው መንገድ ይወጡ የለምን?በጎ ነገር የሚያቅዱ ግን ፍቅርንና ታማኝነትን ያተርፋሉ።

23. ለፍተው የሠሩት ሁሉ ትርፍ ያስገኛል፤ከንቱ ወሬ ግን ወደ ድኽነት ያመራል።

24. ጠቢባን ብልጥግና ዘውዳቸው ነው፤የተላሎች ተላላነት ግን ፍሬው ከንቱነት ነው።

25. እውነተኛ ምስክር ሕይወት ያድናል፤ሐሰተኛ ምስክር ግን አባይ ነው።

26. እግዚአብሔርን የሚፈራ ጽኑ አምባ አለው፤ልጆቹም መጠጊያ ይኖራቸዋል።

27. እግዚአብሔርን መፍራት የሕይወት ምንጭ ነው፤ሰውን ከሞት ወጥመድ ያድነዋል።

28. የሕዝብ ብዛት የንጉሥ ክብር ሲሆን፣የዜጐች ማነስ ግን ለገዥ መጥፊያው ነው።

29. ታጋሽ ሰው ትልቅ ማስተዋል አለው፤ግልፍተኛ ሰው ግን ቂልነትን ይገልጣል።

30. ሰላም ያለው ልብ ለሰውነት ሕይወት ይሰጣል፤ቅናት ግን ዐጥንትን ያነቅዛል።

31. ድኾችን የሚያስጨንቅ ፈጣሪያቸውን ይንቃል፤ለተቸገሩ የሚራራ ሁሉ ግን አምላክን ያከብራል።

32. ክፉዎች በክፋታቸው ይወድቃሉ፤ጻድቃን ግን በሞት ጊዜ እንኳ መጠጊያ አላቸው።

33. ጥበብ በአስተዋዮች ልብ ታድራለች፤በተላሎች መካከል ራሷን ትገልጣለች።

34. ጽድቅ ሕዝብን ከፍ ከፍ ታደርጋለች፤ኀጢአት ግን ለየትኛውም ሕዝብ ውርደት ነው።