ምዕራፎች

  1. 1
  2. 2
  3. 3
  4. 4
  5. 5
  6. 6
  7. 7
  8. 8
  9. 9
  10. 10
  11. 11
  12. 12
  13. 13
  14. 14
  15. 15
  16. 16
  17. 17
  18. 18
  19. 19
  20. 20
  21. 21
  22. 22
  23. 23
  24. 24
  25. 25
  26. 26
  27. 27
  28. 28
  29. 29
  30. 30
  31. 31

ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ምሳሌ 29 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

1. ከብዙ ተግሣጽ በኋላ ዐንገቱን የሚያደነድን ሰው፣በድንገት ይጠፋል፤ መዳኛም የለውም።

2. ጻድቃን ሥልጣን ሲይዙ ሕዝብ ሐሤት ያደርጋል፤ክፉዎች ሲገዙ ግን ሕዝብ ያቃስታል።

3. ጥበብን የሚወድ ሰው አባቱን ደስ ያሰኛል፤የአመንዝራዎች ወዳጅ ግን ሀብቱን ያባክናል።

4. ፍትሕን በማስፈን ንጉሥ አገርን ያረጋጋል፤ጒቦ ለማግኘት የሚጐመጅ ግን ያፈራርሳታል።

5. ባልንጀራውን የሚሸነግል፣ለገዛ እግሩ መረብ ይዘረጋል።

6. ክፉ ሰው በራሱ ኀጢአት ይጠመዳል፤ጻድቅ ግን ይዘምራል፤ ደስም ይለዋል።

7. ጻድቅ ለድኾች ፍትሕ ይጨነቃል፤ክፉ ሰው ግን ደንታ የለውም።

8. ተሳዳቢዎች ከተማን ያውካሉ፤ጠቢባን ግን ቊጣን ያበርዳሉ።

9. ጠቢብ ሰው ከተላላ ጋር ወደ ሸንጎ ቢሄድ፣ተላላ ይቈጣል፤ ያፌዛል፤ ሰላምም አይኖርም።

10. ደም የተጠሙ ሰዎች ሐቀኛን ሰው ይጠላሉ፤ቅን የሆነውንም ለመግደል ይሻሉ።

11. ተላላ ሰው ቊጣውን ያለ ገደብ ይለቀዋል፤ጠቢብ ሰው ግን ራሱን ይቈጣጠራል።

12. ገዥ የሐሰት ወሬ የሚሰማ ከሆነ፣ሹማምቱ ሁሉ ክፉዎች ይሆናሉ።

13. ድኻውና ጨቋኙ የጋራ ነገር አላቸው፤ እግዚአብሔር ለሁለቱም የዐይን ብርሃንን ሰጥቶአቸዋል።

14. ንጉሥ ለድኻ ትክክለኛ ፍርድ ቢሰጥ፣ዙፋኑ ዘላለም ጸንቶ ይኖራል።

15. የተግሣጽ በትር ጥበብን ታጐናጽፋለች፤መረን የተለቀቀ ልጅ ግን እናቱን ያሳፍራል።

16. ክፉዎች ሥልጣን ሲይዙ ኀጢአት ይበዛል፤ጻድቃን ግን የእነርሱን ውድቀት ያያሉ።

17. ልጅህን ቅጣው፤ ሰላም ይሰጥሃል፤ነፍስህንም ደስ ያሰኛታል።

18. ራእይ በሌለበት ሕዝብ መረን ይሆናል፤ሕግን የሚጠብቅ ግን የተባረከ ነው።

19. አገልጋይ በቃል ብቻ ሊታረም አይችልም፤ቢያስተውለውም እንኳ በጀ አይልም።

20. በችኰላ የሚናገርን ሰው ታያለህን?ከእርሱ ይልቅ ተላላ ተስፋ አለው።

21. ሰው አገልጋዩን ከልጅነቱ ጀምሮ ቢያቀማጥል፣የኋላ ኋላ ሐዘን ያገኘዋል።

22. ቊጡ ሰው ጠብን ይጭራል፤ግልፍተኛም ብዙ ኀጢአት ይሠራል።

23. ሰውን ትዕቢቱ ያዋርደዋል፤ ትሑት መንፈስ ያለው ግን ክብርንይጐናጸፋል።

24. የሌባ ግብረ አበር የገዛ ራሱ ጠላት ነው፤የመሐላውን ርግማን እየሰማ ጭጭ ይላል።

25. ሰውን መፍራት ወጥመድ ነው፤ በእግዚአብሔር የሚታመን ግን በሰላም ይኖራል።

26. ብዙዎች በገዥ ፊት ተደማጭነት ማግኘት ይሻሉ፤ሰው ፍትሕ የሚያገኘው ግን ከእግዚአብሔር ዘንድ ነው።

27. ጻድቃን አታላዮችን ይጸየፋሉ፤ክፉዎችም ቅኖችን ይጠላሉ።