ምዕራፎች

  1. 1
  2. 2
  3. 3
  4. 4
  5. 5
  6. 6
  7. 7
  8. 8
  9. 9
  10. 10
  11. 11
  12. 12
  13. 13
  14. 14
  15. 15
  16. 16
  17. 17
  18. 18
  19. 19
  20. 20
  21. 21
  22. 22
  23. 23
  24. 24
  25. 25

ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

2 ነገሥት 23 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

ኢዮስያስ ኪዳኑን ዐደሰ

1. ከዚያም ንጉሡ የይሁዳንና የኢየሩሳሌምን ሽማግሌዎች ሁሉ ጠራ።

2. የይሁዳን ሰዎች ሁሉ፣ የኢየሩሳሌምን ከተማ ነዋሪዎች በሙሉ፣ ካህናቱንና ነቢያቱን ሁሉ ከልጅ እስከ ዐዋቂ አንድም ሰው ሳይቀር ይዞአቸው ወደ እግዚአብሔር ቤተ መቅደስ መጣ። በእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ የተገኘውንም የኪዳኑን መጽሐፍ ቃል በጆሮአቸው እንዲሰሙት በሙሉ አነበበላቸው።

3. ንጉሡም በዐምደ ወርቁ አጠገብ በእግዚአብሔር ፊት ቆሞ እግዚአብሔርን እንደሚከተል ትእዛዞቹን፣ ደንቦቹን፣ ሥር ዐቶቹን በፍጹም ልቡ፣ በፍጹምም ነፍሱ እንደሚጠብቅ፣ በዚህም መጽሐፍ የተጻፈውን ኪዳን እንደሚያጸና በእግዚአብሔር ፊት ኪዳኑን አደሰ፤ ከዚያም ሕዝቡ ሁሉ ለኪዳኑ ያላቸውን ታማኝነት አረጋገጡ።

4. ንጉሡም ለበኣል፣ ለአሼራና ለሰማይ ከዋክብት ሰራዊት ሁሉ የተሠሩትን የመገልገያ ዕቃዎች በሙሉ፣ ከእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ እንዲያወጡ ሊቀ ካህናቱን ኬልቅያስን በሁለተኛ ማዕረግ ያሉትን ካህናትና የቤተ መቅደሱን በር ጠባቂዎች አዘዘ። ዕቃዎቹንም ከኢየሩሳሌም ውጭ በቄድሮን ሸለቆ ሜዳ ላይ አቃጠላቸው፤ ዐመዱንም ወደ ቤቴል ወሰደው።

5. በይሁዳ ከተሞችና በኢየሩሳሌም ዙሪያ በሚገኙ ኰረብቶች ላይ ዕጣን እንዲያጥኑ የይሁዳ ነገሥታት የሾሙአቸውን የጣዖት ካህናት አባረረ እንዲሁም ለበኣል፣ ለፀሓይና ለጨረቃ፣ ለስብስብ ከዋክብትና ለመላው የሰማይ ከዋክብት ሰራዊት የሚያጥኑትን አስወገደ።

6. የአሼራንም ምስል ዐምድ ከእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ አውጥቶ ከኢየሩሳሌም ውጭ ወዳለው ወደ ቄድሮን ሸለቆ ወስዶ አቃጠለው፤ አድቅቆ ፈጭቶም በሕዝቡ መቃብር ላይ በተነው።

7. እንዲሁም ስለ አምልኮ ባዕድ ሥርዐት በእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ ውስጥ የቤተ ጣዖት ወንደቃዎችን ክፍሎችና ሴቶች ለአሼራ መጋረጃ የሚፈትሉባቸውን ክፍሎች አፈረሰ።

8. ኢዮስያስ የቤተ ጣዖት ካህናትን ሁሉ ከይሁዳ ከተማ ወደ ኢየሩሳሌም አወጣቸው፤ ከጌባ ጀምሮ እስከ ቤርሳቤህ ድረስ፣ ካህናቱ ዕጣን ያጥኑባቸው የነበሩትን የኰረብታ ማምለኪያ ስፍራዎችን አረከሰ። ከከተማዪቱ በር በስተ ግራ በኩል፣ በከተማዪቱ ገዥ በኢያሱ በር መግቢያ አጠገብ የነበሩትን የበሮቹን ማምለኪያ ስፍራዎች አፈረሰ።

9. የየኰረብታው ማምለኪያ ካህናት ኢየሩሳሌም ባለው በእግዚአብሔር መሠዊያ ላይ ባያገለግሉም እንኳ ከካህናት ወንድሞቻቸው ጋር እርሾ ያልነካው ቂጣ ይበሉ ነበር።

10. በሄኖም ሸለቆ የነበረውን ቶፌት የተባለውን ማምለኪያ አረከሰ፤ ይኸውም ማንም ሰው ወንድ ወይም ሴት ልጁን ለሞሎክ በእሳት የሚቃጠል መሥዋዕት አድርጎ እንዳያቀርብበት ነው።

11. የይሁዳ ነገሥታት ወደ እግዚአብሔር ቤተ መቅደስ መግቢያ ላይ ለፀሓይ አምልኮ የሰጡአቸውን ፈረሶች ከዚያ አስወገደ። እነዚህም ናታን ሜሌክ በተባለ በአንድ ሹም ቤት አጠገብ በአደባባዩ ላይ ነበሩ። ኢዮስያስም ለፀሐይ አምልኮ የተሰጡትን ሠረገሎች አቃጠለ።

12. የይሁዳ ነገሥታት በላይኛው የአካዝ እልፍኝ አጠገብ በሰገነቱ ላይ ያቆሟቸውን መሠዊያዎች፣ ምናሴም በሁለቱ የእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ አደባባዮች ላይ ያሠራቸውን መሠዊያዎች አስወገደ፤ ስብርብራቸውን አወጣ፤ ድቃቂውንም አንሥቶ ወደ ቄድሮን ሸለቆ ጣለው።

13. እንዲሁም ከኢየሩሳሌም በስተ ምሥራቅ ከርኵሰት ኰረብታ በስተ ደቡብ የነበሩትን የእስራኤል ንጉሥ ሰሎሞን ለሲዶናውያን የርኵሰት አምላክ ለአስታሮት፣ ለሞዓብ ሕዝቦች የርኵሰት አምላክ ለካሞሽ፣ ለአሞን ሕዝቦች የርኵሰት አምላክ ለሞሎክ ያሠራቸውን የኰረብታ ላይ ማምለኪያዎች ንጉሡ አረከሰ።

14. አሁንም ኢዮስያስ ማምለኪያ የድንጋይ ሐውልቶችን ሰባበረ፤ የአሼራን ምስል ዐምዶች ቈራረጠ፤ ስፍራውንም በሙታን ዐጥንት ሞላው።

15. እስራኤልን ባሳተው በናባጥ ልጅ በኢዮርብዓም የተሠራውን መሠዊያ፣ በቤቴል የነበረውን ያን የኰረብታ ማምለኪያ ስፍራ፣ መሠዊያው ያለበትን ያን የኰረብታ ማምለኪያ ስፍራ እንኳ እንደዚሁ አፈረሰ፤ ድንጋዮቹን ሰባበረ፤ እንደ ዱቄትም አደቀቃቸው፤ የአሼራንም ምስል ዐምድ አቃጠለ።

16. ኢዮስያስ ዘወር ሲል በኰረብታው ላይ የነበሩትን መቃብሮች አየ፤ ዐፅሞቹንም ከየመቃብሩ አስወጣ፤ ያ የእግዚአብሔር ሰው አስቀድሞ እንደ ተናገረው፣ የእግዚአብሔር ቃል ይፈጸም ዘንድ፣ መሠዊያውን ለማርከስ ሲል ዐፅሞቹን በላዩ ላይ አቃጠለበት።

17. ንጉሡም፣ “ያ የማየው የመቃብር ሐውልት የማን ነው?” ሲል ጠየቀ የከተማዪቱም ሰዎች፣ “ከይሁዳ መጥቶ አሁን አንተ ያደረግኸውን ነገር ሁሉ በቤቴል መሠዊያ ላይ እንደሚደርስ የተናገረ የዚያ የእግዚአብሔር ሰው መቃብር ነው” አሉት።

18. ኢዮስያስም፣ “በሉ እንዳለ ተዉት፤ ዐፅሙን ማንም ሰው ከቦታው እንዳያንቀሳ ቅሰው” አለ፤ ስለዚህ የእርሱንና ከሰማርያ የመጣውን ነቢይ ዐፅም ሳይነኩ እንዳለ ተውት።

19. ኢዮስያስም በቤቴል እንዳደረገው ሁሉ በሰማርያም ከተሞች ኰረብቶች ላይ የእስራኤል ነገሥታት አሠርተዋቸው የነበሩትንና እግዚአብሔርን ያስቈጡበትን ቤተ ጣዖቶች ሁሉ አስወገደ፤ አረከሳቸውም።

20. ኢዮስያስ እነዚያን የየኰረብታውን ማምለኪያ ቦታ ካህናትን ሁሉ፣ በየመሠዊያው ላይ ዐረዳቸው፤ በመሠዊያዎቹ ላይ የሰው ዐፅም አቃጠለ፣ ከዚያም ወደ ኢየሩሳሌም ተመለሰ።

21. ንጉሡም መላውን ሕዝብ፣ “በዚህ በኪዳኑ መጽሐፍ በተጻፈው መሠረት የአምላካችሁን የእግዚአብሔርን ፋሲካ አክብሩ” ብሎ አዘዘ።

22. እስራኤልን ከመሩ ከመሳፍንት ዘመን ጀምሮ፣ በእስራኤልና በይሁዳ ነገሥታት ዘመን ሁሉ፣ እንደዚህ ያለ ፋሲካ መቼም ተከብሮ አያውቅም።

23. በኢዮስያስ ዘመነ መንግሥት በዐሥራ ስምንተኛው ዓመት ግን ይህ ፋሲካ በኢየሩሳሌም ለእግዚአብሔር ተከበረ።

24. ከዚህም በቀር ኢዮስያስ ሙታን አነጋጋሪዎችንና መናፍስት ጠሪዎችን፣ የየቤተ ሰውን አማልክት፣ ጣዖታትን እንዲሁም በይሁዳና በኢየሩሳሌም የተገኙትን ሌሎች አስጸያፊ ነገሮች ሁሉ አስወገደ፤ ይህን ያደረገውም ካህኑ ኬልቅያስ ከእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ ባገኘው መጽሐፍ የተጻፈው የሕጉ ቃል ተፈጻሚነት እንዲኖረው ለማድረግ ነው።

25. በሙሴ ሕግ በተጻፈው መሠረት በፍጹም ልቡ፣ በፍጹም ነፍሱ፣ በፍጹም ኀይሉ ወደ እግዚአብሔር የተመለሰ፣ እንደ ኢዮስያስ ያለ ንጉሥ፣ ከእርሱ በፊትም ሆነ ከእርሱ በኋላ ፈጽሞ አልተነሣም።

26. ይህም ሆኖ እንኳ ለቊጣ እንዲነሣሣ ምናሴ ካደረጋቸው ነገሮች ሁሉ የተነሣ፣ እግዚአብሔር በይሁዳ ላይ ከነደደው ከአስፈሪው ቊጣው ገና አልበረደም ነበር።

27. ስለዚህ እግዚአብሔር፣ “እስራኤልን እንዳስወገድሁ ሁሉ ይሁዳንም ከፊቴ አስወግዳለሁ የመረጥኋትን ከተማ ኢየሩሳሌምንና፣ ‘ስሜ በዚያ ይሆናል’ ብዬ የተናገር ሁለትን ይህን ቤተ መቅደስ እተዋለሁ” አለ።

28. በኢዮስያስ ዘመነ መንግሥት የተከናወነው ሌላው ሥራ፣ የፈጸመውም ሁሉ በይሁዳ ነገሥታት ታሪክ ተጽፎ የሚገኝ አይደለምን?

29. ኢዮስያስ ንጉሥ በነበረበት ዘመን የግብፅ ንጉሥ ፈርዖን ኒካዑ የአሦርን ንጉሥ ለመርዳት ወደ ኤፍራጥስ ወንዝ ወጥቶ ነበር፤ ንጉሥ ኢዮስያስም ጦርነት ሊገጥመው ወጣ፤ ሆኖም ፈርዖን ኒካዑ ፊት ለፊት ገጥሞት መጊዶ ላይ ገደለው።

30. የኢዮስያስም አገልጋዮች ከመጊዶ ሬሳውን በሠረገላ ወደ ኢየሩሳሌም አምጥተው በገዛ መቃብሩ ቀበሩት። የአገሩም ሰዎች የኢዮስያስን ልጅ ኢዮአክስን ወሰዱት፤ ቀብተውም በአባቱ እግር አነገሡት።

የይሁዳ ንጉሥ ኢዮአክስ

31. ኢዮአክስ ሲነግሥ ዕድሜው ሃያ ሦስት ዓመት ነበር፤ እርሱም በኢየሩሳሌም ተቀምጦ ሦስት ወር ገዛ። እናቱ አሚጣል ትባላለች፤ እርሷም የልብና ሰው የኤርምያስ ልጅ ነበረች።

32. አባቶቹ እንዳደረጉ ሁሉ፣ እርሱም በእግዚአብሔር ፊት ክፉ አደረገ።

33. በኢየሩሳሌም ተቀምጦ እንዳይ ገዛም ፈርዖን ኒካዑ በሐማት ምድር ሪብላ በምትባል ቦታ በሰንሰለት አሰረው፤ በይሁዳም ላይ መቶ መክሊት ብርና አንድ መክሊት ወርቅ ግብር ጣለበት።

34. ፈርዖን ኒካዑ የኢዮስያስን ልጅ ኤልያቄምን በአባቱ በኢዮስያስ እግር አነገሠው፤ ኤልያቄም የተባለ ስሙንም ኢዮአቄም ብሎ ለወጠው። ነገር ግን ኢዮአክስን በምርኮ ወደ ግብፅ ወሰደው፤ እርሱም በዚያ ሞተ።

35. ኢዮአቄምም ፈርዖን ኒካዑ የጠየቀውን ብርና ወርቅ ከፈለ፤ ይህን ለማድረግም የመሬት ግብር ጣለ፤ የአገሩም ሰዎች እንደ ገቢው መጠን ብሩንና ወርቁን እንዲከፍሉ አደረገ።

ኢዮአቄም የይሁዳ ንጉሥ

36. ኢዮአቄም ሲነግሥ ዕድሜው ሃያ አምስት ዓመት ነበር፤ በኢየሩሳሌም ተቀምጦም ዐሥራ አንድ ዓመት ገዛ። እናቱ ዘቢዳ ትባላለች፤ እርሷም የሩማ ተወላጅ የፈዳያ ልጅ ነበረች።

37. ኢዮአቄም አባቶቹ እንደ አደረጉት ሁሉ፣ እርሱም በእግዚአብሔር ፊት ክፉ ነገር አደረገ።