ምዕራፎች

  1. 1
  2. 2
  3. 3
  4. 4
  5. 5
  6. 6
  7. 7
  8. 8
  9. 9
  10. 10
  11. 11
  12. 12
  13. 13
  14. 14
  15. 15
  16. 16
  17. 17
  18. 18
  19. 19
  20. 20
  21. 21
  22. 22
  23. 23
  24. 24
  25. 25

ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

2 ነገሥት 19 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

ኢየሩሳሌም ከጠላት እጅ እንደምትድን አስቀድሞ መነገሩ

1. ንጉሥ ሕዝቅያስ ይህን ሲሰማ ልብሱን ቀደደ፤ ማቅ ለብሶም ወደ እግዚአብሔር ቤተ መቅደስ ገባ።

2. ከዚያም የቤተ መንግሥቱን አዛዥ ኤልያቄምን፣ ጸሓፊውን ሳምናስንና ዋና ዋናዎቹን ካህናት ማቅ ለብሰው ወደ አሞጽ ልጅ ወደ ነቢዩ ኢሳይያስ እንዲሄዱ ሁሉንም ላካቸው።

3. እነርሱም እንዲህ አሉት፤ “ሕዝቅያስ የሚለው ይህ ነው፤ ‘እንግዲህ ይህች ዕለት የመከራ፣ የዘለፋና የውርደት ቀን ናት፤ ይህችም ቀን ልጆች ሊወለዱ ምጥ እንዳፋፋመበት፣ ነገር ግን ለመገላገል ዐቅም እንደታጣበት ሰዓት ናት።

4. ሕያው እግዚአብሔርን ያንቋሽሽ ዘንድ በጌታው በአሦር ንጉሥ የተላከውን የጦር አዛዡን ቃል ሁሉ እግዚአብሔር አምላክህ ሰምቶ ይሆናልና፣ ስለሰማውም ቃል እግዚአብሔር እንዲገሥጸው በሕይወት ስለተረፉት ወገኖቻችን እባክህ ጸልይ።”

5. የንጉሥ ሕዝቅያስ ሹማምት ወደ ኢሳይያስ በመጡ ጊዜ፣

6. ኢሳይያስ እንዲህ አላቸው፤ “ለጌታችሁ እንዲህ ብላችሁ ንገሩት፤ ‘እንግዲህ እግዚአብሔር የሚለው ይህ ነው፤ “የአሦር ንጉሥ አገልጋዮች በእኔ ላይ የወረወሯቸውን የስድብ ቃላት በመስማትህ አትፍራ።

7. እነሆ፣ አንድ ዐይነት መንፈስ አሳድርበታለሁ፤ የሆነ ወሬም ሲሰማ ወደ አገሩ ይመለሳል፤ እዚያም በሰይፍ እንዲወድቅ አደርገዋለሁ።’ ”

8. የጦር አዛዡም የአሦር ንጉሥ ለኪሶን ትቶ መሄዱን ሲሰማ ተመለሰ፤ ንጉሡንም ልብናን ሲወጋ አገኘው።

9. በዚህም ጊዜ የግብፅ ንጉሥ ኢትዮጵያዊው ቲርሐቅ፣ ሊወጋው በመገሥገሥ ላይ መሆኑን ሰናክሬም ሰማ፤ ስለዚህ ወደ ሕዝቅያስ እንደ ገና እንዲህ ሲል መልእክተኞች ላከ፤

10. “ሂዱና ለይሁዳ ንጉሥ ለሕዝቅያስ እንዲህ በሉት፤ ‘የምትመካበት አምላክ፣ “ኢየሩሳሌም በአሦር ንጉሥ እጅ አትወድቅም” በማለት እንዳያታልልህ።

11. መቼም የአሦር ነገሥታት በአገሮች ሁሉ ላይ ምን እንዳደረጉ ሰምተሃል፤ ፈጽሞ አጥፍተዋቸዋል፤ ታዲያ አንተስ ከዚህ የምታመልጥ ይመስልሃልን?

12. የቀድሞ አባቶቼ ያጠፏቸውን ሕዝቦች ማለትም ጎዛንን፣ ካራንን፣ ራፊስን እንዲሁም በተላሳር የነበሩትን የዔድንን ሰዎች አማልክታቸው አድነዋቸዋልን?

13. ለመሆኑ የሐማትና የአርፋድ ነገሥታት የት አሉ? የሴፈርዋይም ከተማ ንጉሥስ የት አለ? ደግሞስ የሄና ወይም የዒዋ ነገሥታት የት አሉ?

የሕዝቅያስ ጸሎት

14. ሕዝቅያስም ደብዳቤውን ከመልእክተኞቹ ተቀብሎ አነበበው፤ ከዚያም ወደ እግዚአብሔር ቤተ መቅደስ ወጥቶ ደብዳቤውን በእግዚአብሔር ፊት ዘረጋው።

15. ከዚያም ሕዝቅያስ እንዲህ ሲል ወደ እግዚአብሔር ጸለየ፤ “በኪሩቤል ላይ በዙፋንህ የተቀመጥህ የእስራኤል አምላክ እግዚአብሔር ሆይ፤ በምድር ነገሥታት ሁሉ ላይ አምላክ አንተ ብቻ ነህ፤ ሰማይንና ምድርን የፈጠርህም አንተ ነህ።

16. እግዚአብሔር ሆይ፤ አሁንም ጆሮህን አዘንብልና ስማ፤ እግዚአብሔር ሆይ፤ ዐይንህንም ክፈትና እይ፤ ሰናክሬም ሕያው እግዚአብሔርን ይሰድብ ዘንድ የላከውንም ቃል አድምጥ።

17. “እግዚአብሔር ሆይ፤ የአሦር ነገሥታት እነዚህን አሕዛብንና ምድራቸውን በርግጥ አጥፍተዋል።

18. አማልክቶቻቸውን በእሳት ውስጥ ጥለው አቃጥለዋቸዋል፤ በሰው እጅ የተሠሩ ዕንጨትና ደንጊያ ብቻ እንጂ አማልክት አልነበሩምና።

19. አሁንም እግዚአብሔር አምላካችን ሆይ፤ የምድር መንግሥታት ሁሉ እግዚአብሔር አንተ ብቻ አምላክ መሆንህን እንዲያውቁ፣ ከእጁ አድነን።”

ኢሳይያስ ስለ ሰናክሬም መውደቅ ትንቢት ተናገረ

20. ከዚያም የአሞጽ ልጅ ኢሳይያስ ወደ ሕዝቅያስ እንዲህ ሲል መልእክት ላከ፤ “የእስራኤል አምላክ እግዚአብሔር የሚለው ይህ ነው፤ ‘በአሦር ንጉሥ በሰናክሬም ላይ ወደ እኔ ያቀረብኸውን ልመና ሰምቻለሁ።

21. እንግዲህ እግዚአብሔር በእርሱ ላይ የተናገረው ቃል ይህ ነው፤“ ‘ድንግሊቱ የጽዮን ልጅ፣ትንቅሃለች፤ ታቃልልሃለችም፤የኢየሩሳሌም ልጅ፣አንተ በላይዋ ስትበር ራሷን ትነቀንቅብሃለች።

22. ለመሆኑ የሰደብኸውና ያቃለልኸው ማንን ነው?ድምፅህንስ ከፍ ያደረግኸው?ዐይንህንስ በኵራት ያነሣኸው በማን ላይ ነው?በእስራኤል ቅዱስ ላይ ነው እንዴ?

23. በመልእክተኞችህ አማካይነት፣በአምላክ ላይ የስድብ መዓት አውርደሃል፤እንዲህም ብለሃል፤“በብዙ ሠረገሎቼ፣የተራሮቹን ከፍታ፣የሊባኖስንም የመጨረሻ ጫፍ ወጥቻለሁ፤ረጃጅም ዝግባዎቹን፣ምርጥ የሆኑ ጥዶቹንም ቈርጫለሁ፤ወደ ሩቅ ዳርቻዎቹ፣ወደ ውብ ደኖቹም ደርሻለሁ።”

24. “በሌሎች አገሮችም የውሃ ጒድጓዶች ቈፍሬአለሁ፤በዚያም ውሃ ጠጥቻለሁ፤በእግሬ ጫማዎችም፣የግብፅን ምንጮች ሁሉ ረግጬ አድርቄአለሁ።”

25. “ ‘ከብዙ ጊዜ በፊት፣ይህን እኔ እንዳደረግሁት አልሰማህም ነበርን?ዕቅዱን ገና ድሮ አውጥቼ፣አሁን ግን እንዲፈጸም አደረግሁት፤ይህም የተመሸጉትን ከተሞች፣አንተ የድንጋይ ክምር ማድረግህ ነው።

26. የሚኖሩባቸውም ሰዎች ኀይላቸው ተሟጦ አልቆአል፤ደንግጠውም የኀፍረት ማቅ ለብሰዋል፤ሜዳ ላይ እንደ በቀለ ተክል፣ገና እንዳልጠነከረ የቡቃያ ሥር፣በቤት ጣራ ላይ በቅሎ፣ገና ሳያድግ እንደ ጠወለገ ሣርም ሆነዋል።

27. “ ‘የት እንደምትቀመጥ፣መቼ መጥተህ መቼ እንደምትሄድ፣በእኔም ላይ የተቈጣኸውን ቊጣ ዐውቃለሁ።

28. በእኔ ላይ በመቈጣትህ፣ንቀትህም ወደ ጆሮዬ ስለ ደረሰ፣ስናጋዬን በአፍንጫህ አደርጋለሁ፤ልጓሜን በአፍህ አገባለሁ፤በመጣህበትም መንገድእንድትመለስ አደርጋለሁ።’

29. “ሕዝቅያስ ሆይ፤ ምልክቱ ይህ ነው፤“በዚህ ዓመት በገዛ እጁ የበቀለውን፣በሚመጣው ዓመት ደግሞ የገቦውን እህል ትበላላችሁ፤በሦስተኛው ዓመት ግን ትዘራላችሁ፤ ታጭዳላችሁ፤ወይንም ትተክላላችሁ፤ ፍሬውንም ትበላላችሁ።

30. አሁንም ከዳዊት ቤት የተረፉት፣ሥራቸውን ወደ ታች ይሰዳሉ፤ ወደ ላይም ፍሬ ያፈራሉ።

31. ከኢየሩሳሌም በሕይወት የተረፉት፣ከጽዮን ተራራም ከሞት ያመለጡት ይወጣሉና። የእግዚአብሔር ቅናት ይህን ታደርጋለች።

32. “እንግዲህ እግዚአብሔር ስለ አሦር ንጉሥ የሚለው ይህ ነው፤“ወደዚች ከተማ ፈጽሞ አይገባም፤አንዲትም ፍላጻ አይወረውርባትም፤ጋሻ አንግቦ ወደ እርሷ አይቀርብም፤በዐፈርም ቊልል አይከባትም።

33. በመጣበት መንገድ ተመልሶ ይሄዳል፤ተመልሶ ይሄዳታል እንጂ ወደዚች ከተማ ፈጽሞ አይገባም፤ይላል እግዚአብሔር።

34. ስለ ራሴና ስለ ባሪያዬም ስለ ዳዊት ስል፣ይህችን ከተማ አድናት ዘንድ እጋርዳታለሁ።

35. በዚያችም ሌሊት የእግዚአብሔር መልአክ ወጥቶ ከአሦራውያን ሰፈር መቶ ሰማንያ አምስት ሺህ ሰው ገደለ። በማግስቱም ሰዎቹ ሲነቁ ቦታው ሬሳ በሬሳ ሆኖ ተገኘ።

36. የአሦር ንጉሥ ሰናክሬም ከዚያ ተነሥቶ ሄደ፤ ወደ ነነዌም ተመልሶ በዚያ ተቀመጠ።

37. አንድ ቀንም ናሳራክ በተባለው አምላኩ ቤተ ጣዖት ገብቶ በመስገድ ላይ ሳለ፣ አድራሜሌክና ሳራሳር የተባሉ ልጆቹ በሰይፍ ገደሉት፤ ከዚያም አምልጠው ወደ አራራት ሸሹ። ልጁ አስራዶንም በእግሩ ተተክቶ ነገሠ።