ምዕራፎች

  1. 1
  2. 2
  3. 3
  4. 4
  5. 5
  6. 6
  7. 7
  8. 8
  9. 9
  10. 10
  11. 11
  12. 12
  13. 13
  14. 14
  15. 15
  16. 16
  17. 17
  18. 18
  19. 19
  20. 20
  21. 21
  22. 22
  23. 23
  24. 24
  25. 25
  26. 26
  27. 27
  28. 28
  29. 29
  30. 30
  31. 31

ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

1 ሳሙኤል 24 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

ዳዊት ሳኦልን ከመግደል ታቀበ

1. ሳኦል ፍልስጥኤማውያንን ከማሳደድ ከተመለሰ በኋላ፣ “እነሆ፤ ዳዊት በዓይንጋዲ ምድረ በዳ አለ” ብለው ነገሩት።

2. ስለዚህ ሳኦል ከመላው እስራኤል የተመረጡ ሦስት ሺህ ሰዎችን ይዞ ዳዊትንና ሰዎቹን ለመፈለግ “የሜዳ ፍየሎች ዐለት” ወደተባለው ቦታ አቅራቢያ ሄደ።

3. ሳኦልም በመንገድ ዳር ወዳለው ወደ አንድ የበጎች ማደሪያ በደረሰ ጊዜ፣ ዋሻ አግኝቶ ወገቡን ሊሞክር ወደዚያ ገባ። ዳዊትና ሰዎቹም ከዋሻው በውስጠኛው ቦታ ተቀምጠው ነበር።

4. የዳዊት ሰዎችም ዳዊትን፣ “እግዚአብሔር፣ ‘የወደድኸውን ታደርግበት ዘንድ ጠላትህን በእጅህ አሳልፌ እሰጥሃለሁ’ ብሎ ለአንተ የተናገረው ቀን ዛሬ ነው” አሉት። ዳዊትም በልቡ እየተሳበ ሄዶ የሳኦልን ልብስ ጫፍ ማንም ሳያውቅ ቈርጦ ወሰደ።

5. ዳዊት የሳኦልን ልብስ ጫፍ በመቊረጡ ልቡ በሐዘን ተመታ።

6. ለሰዎቹም፣ “እግዚአብሔር በቀባው በጌታዬ ላይ እንዲህ ያለውን ነገር ከማድረግና እግዚአብሔር የቀባው ስለ ሆነም እጄን በእርሱ ላይ ከማንሣት እግዚአብሔር ይጠብቀኝ” አላቸው።

7. ዳዊት ሰዎቹን በዚህ ቃል ገሠጻቸው፤ በሳኦል ላይ አደጋ እንዲያደርሱበትም አልፈቀደላቸውም። ሳኦልም ከዋሻው ወጥቶ ሄደ።

8. ከዚያም ዳዊት ከዋሻው ወጥቶ ሳኦልን፣ “ጌታዬ ንጉሥ ሆይ!” ብሎ ጠራው። ሳኦልም ወደ ኋላው ዞር ባለ ጊዜ፣ ዳዊት ወደ መሬት ጐንበስ ብሎ እጅ ሲነሣው ተመለከተ፤

9. ዳዊትም ሳኦልን እንዲህ አለው፤ “ሰዎች፣ ‘እነሆ፤ ዳዊት ክፉ ነገር ሊያደርግብህ ይፈልጋል’ ሲሉ ለምን ትቀበላቸዋለህ?

10. በዛሬው ዕለት በዋሻው ውስጥ እግዚአብሔር አንተን እንዴት አድርጎ በእጄ ላይ እንደ ጣለህ እነሆ፤ በገዛ ዐይንህ አይተሃል፤ አንዳንዶች እንድገድልህ ገፋፍተውኝ ነበር፤ እኔ ግን፣ ‘እግዚአብሔር በቀባው በጌታዬ ላይ እጄን አላነሣም’ በማለት ራራሁልህ።

11. አባቴ ሆይ፤ የልብስህ ቍራጭ ይኸው በእጄ ላይ ተመልከት! የልብስህን ጫፍ ቈረጥሁ እንጂ አንተን አልገደልሁህም። አሁንም ክፋት ወይም ዐመፅ አለመፈጸሜን ዕወቅልኝ፤ ተረዳልኝም፤ እኔ ክፉ አልሠራሁብህም፤ አንተ ግን ሕይወቴን ለማጥፋት እያሳደድኸኝ ነው።

12. እግዚአብሔር በአንተና በእኔ መካከል ይፍረድ። ክፉ ስላደረግህብኝ እግዚአብሔር ይበቀልህ እንጂ፣ እጄስ በአንተ ላይ አትሆንም፤

13. በጥንት አባባል፣ ‘ከክፉ አድራጊዎች ክፉ ድርጊት ይወጣል’ እንደ ተባለ፤ አሁንም እጄ በአንተ ላይ አትሆንም።

14. “የእስራኤል ንጉሥ የወጣው በማን ላይ ነው? አንተስ የምታሳድደው ማንን ነው? የሞተ ውሻን? ወይስ ቁንጫ?

15. አሁንም እግዚአብሔር ዳኛ ሆኖ በመካከላችን ይፍረድ፤ ጒዳዬን ተመልክቶ እርሱው ይሟገትልኝ፤ እኔንም ከእጅህ ነጻ በማውጣት እውነተኛ መሆኔን ይግለጠው።”

16. ዳዊት ይህን ተናግሮ ሲያበቃ ሳኦል፣ “ልጄ ዳዊት ሆይ፤ ይህ የአንተ ድምፅ ነውን?” ሲል ጠየቀው፤ ጮኾም አለቀሰ።

17. እንዲህም አለ፤ “ክፉ ሳደርግብህ፣ በጎ መልሰህልኛልና፣ አንተ ከእኔ ይልቅ ጻድቅ ነህ።

18. ያደረግህልኝን በጎ ነገር ይኸው ነግረኸኛል፤ እግዚአብሔር እኔን በእጅህ ጥሎኝ ነበር፤ አንተ ግን አልገደልኸኝም።

19. ለመሆኑ ጠላቱን አግኝቶ ጉዳት ሳያደርስበት የሚለቀው ማን ነው? ዛሬ ስላደረግህልኝ ቸርነት እግዚአብሔር ይመልስልህ።

20. እነሆ፤ አንተ በእርግጥ እንደምትነግሥና የእስራኤል መንግሥት በእጅህ እንደምትጸና ዐውቃለሁ።

21. ዘሮቼን እንዳታጠፋ ስሜንም ከአባቴ ቤት እንዳት ደመስስ አሁን በእግዚአብሔር ማልልኝ።”

22. ዳዊትም ለሳኦል ማለለት፤ ከዚያም ሳኦል ወደ ቤቱ ተመለሰ። ዳዊትና ሰዎቹ ግን ወደ ዐምባው ወጡ።