ምዕራፎች

  1. 1
  2. 2
  3. 3
  4. 4
  5. 5
  6. 6
  7. 7
  8. 8
  9. 9
  10. 10
  11. 11
  12. 12
  13. 13
  14. 14
  15. 15
  16. 16
  17. 17
  18. 18
  19. 19
  20. 20
  21. 21
  22. 22
  23. 23
  24. 24
  25. 25
  26. 26
  27. 27
  28. 28
  29. 29
  30. 30
  31. 31

ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

1 ሳሙኤል 30 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

ዳዊት አማሌቃውያንን አጠፋ

1. በሦስተኛው ቀን ዳዊትና ሰዎቹ ጺቅላግ ደረሱ፤ በዚህ ጊዜ አማሌቃውያን ደቡቡን አገርና ጺቅላግን ወረው ነበር፤ ጺቅላግንም ወግተው አቃጥለው ነበር።

2. ሴቶቹን፣ በዚያ የነበሩትን ወጣቶችና ሽማግሌዎቹን ሁሉ ማርከው ወሰዱ፤ የማረኩትንም ይዘው ከመሄድ በስተቀር አንዱንም አልገደሉም ነበር።

3. ዳዊትና ሰዎቹ ወደ ጺቅላግ እንደ ደረሱም፣ እነሆ፤ ከተማዪቱ በእሳት ጋይታ፣ ሚስቶቻቸው፣ ወንዶችና ሴቶች ልጆቻቸው ተማርከው አገኙ።

4. በዚህ ጊዜ ዳዊትና ሰዎቹ ማልቀስ እስከሚያቅታቸው ድረስ ድምፃቸውን ከፍ አድርገው አለቀሱ፤

5. ሁለቱ የዳዊት ሚስቶች ማለትም ኢይዝራኤላዊቷ አኪናሆምና የቀርሜሎሳዊው የናባል ሚስት የነበረችው አቢግያም ተማርከው ነበር።

6. ሰዎቹ ስለ ወንዶችና ሴቶች ልጆቻቸው ነፍሳቸው ተመራ ሊወግሩት ስለ ተመካከሩ ዳዊት በጣም ተጨነቀ፤ ነገር ግን ዳዊት በአምላኩ በእግዚአብሔር በረታ።

7. ከዚያም ዳዊት የአቢሜሌክን ልጅ ካህኑን አብያታርን፣ “ኤፉዱን አምጣልኝ” አለው፤ አብያታርም አመጣለት፤

8. ዳዊትም፣ “ይህን ወራሪ ሰራዊት ልከተለውን?’ እደርስባቸዋለሁን?” ሲል እግዚአብሔርን ጠየቀ። እግዚአብሔርም፣ “በእርግጥ ትደርስባቸዋለህ፤ ምርኮውንም ትመልሳለህ፤ ተከተል” ሲል መለሰለት።

9. ስለዚህ ዳዊትና አብረውት የነበሩት ስድስት መቶ ሰዎች ወደ ቦሦር ወንዝ መጡ፤ ጥቂቶቹም በቦሦር ወንዝ ቈዩ፤

10. ሁለት መቶዎቹ እጅግ ዝለው ስለ ነበር ወንዙን መሻገር አልቻሉምና። ነገር ግን ዳዊትና አራት መቶ ሰዎች መከታተላቸውን ቀጠሉ።

11. እነርሱም በምድረ በዳ አንድ ግብፃዊ አገኙ፤ ወደ ዳዊትም አመጡት፤ የሚጠጣውን ውሃና የሚበላውን ምግብ ሰጡት።

12. እንደዚሁም የበለስ ጥፍጥፍ ቍራሽና ሁለት ደረቅ የወይን ዘለላዎች ሰጡት። ሦስት ቀንና ሦስት ሌሊት ምንም እህል ስላልበላ፣ ውሃም ስላልጠጣ ይህን ከበላ በኋላ ነፍሱ ተመለሰች።

13. ዳዊትም፣ “አንተ የማን ነህ? የመጣኸውስ ከየት ነው?” ብሎ ጠየቀው።እርሱም እንዲህ አለው፤ “እኔ ግብፃዊ ስሆን፣ የአንድ አማሌቃዊ ባሪያ ነኝ፤ ከሦስት ቀን በፊት ታምሜ በነበረበት ጊዜ ጌታዬ ጥሎኝ ሄደ።

14. የከሊታውያንን ደቡብ፣ የይሁዳን ግዛትና የካሌብን ደቡብ ወረርን፤ ጺቅላግንም በእሳት አጋየናት።”

15. ዳዊትም፣ “ታዲያ ወራሪው ሰራዊት ወዳለበት መርተህ ታደርሰኛለህ?” ሲል ጠየቀው።እርሱም፣ “እንደማትገድለኝ ወይም ለጌታዬ አሳልፈህ እንደማትሰጠኝ በእግዚአብሔር ማልልኝ እንጂ እነዚህ ወራሪዎች ወዳሉበት አደርስሃለሁ” አለው።

16. ዳዊትን ወደ ታች መርቶ ባደረሰው ጊዜም፣ ወራሪዎቹ ከፍልስጥኤማውያንና ከይሁዳ ምድር ከወሰዱት ታላቅ ምርኮ የተነሣ በየቦታው ተበታትነው ይበሉ፣ ይጠጡና ይዘፍኑ፣ ይጨፍሩም ነበር።

17. ዳዊት፣ ከዚያች ዕለት ማታ ጀምሮ እስከ ማግሥቱ ምሽት ድረስ ወጋቸው፤ በግመል ተቀምጠው ከሸሹት አራት መቶ ወጣቶች በስተቀር፣ ከመካከላቸው ያመለጠ አንድም አልነበረም።

18. ዳዊት አማሌቃውያን የወሰዱትን ሁሉ አስጣለ፣ ሁለቱንም ሚስቶቹን አስመለሰ።

19. ትንሽም ሆነ ትልቅ፣ ወንዶችም ሆኑ ሴቶች ልጆች፣ ምርኮም ሆነ ሌላ፣ አማሌቃውያን ከወሰዱት ነገር ምንም የጐደለ አልነበረም፤ ዳዊት ሁሉንም አስመለሰ።

20. እንዲሁም ዳዊት የበጉን፣ የፍየሉንና የላሙን መንጋ ሁሉ ወሰደ፤ ሰዎቹም “ይህ የዳዊት ምርኮ ነው” እያሉ መንጋውን ከሌሎች ከብቶች ፊት ለፊት ይነዱ ነበር።

21. ከዚያም ዳዊት፣ እጅግ በመድከማቸው ምክንያት ሊከተሉት ወዳልቻሉት በቦሦር ወንዝ ቀርተው ወደ ነበሩት ወደ ሁለቱ መቶ ሰዎች መጣ፤ እነርሱም ዳዊትንና አብረውት የነበሩትን ሰዎች ለመቀበል ወጡ። ዳዊትና ሰዎቹ ወደ እነርሱ እንደ ቀረቡም ዳዊት ሰላምታ ሰጣቸው።

22. ከዳዊት ተከታዮች ክፉዎቹና ምናምንቴዎቹ ሁሉ ግን፣ “አብረውን ስላልዘመቱ ካመጣነው ምርኮ አናካፍላቸውም፤ ነገር ግን እያንዳንዱ ሚስቱንና ልጆቹን ይዞ መሄድ ይችላል” አሉ።

23. ዳዊትም እንዲህ አለ፤ “ወንድሞቼ ሆይ፤ የጠበቀን፣ የመጣብንንም ወራሪ በእጃችን የጣለልን እግዚአብሔር ነው፤ እርሱ በሰጠን ነገር ይህን ማድረግ አይገባችሁም።

24. የምትሉትን ማን ይቀበላችኋል? ከጓዝ ጋር የቀረው ሰው ድርሻ ለጦርነት ከወጣው ሰው ድርሻ ጋር አይበላለጥም፤ ሁሉም እኩል ይካፈላሉ።”

25. ዳዊትም ከዚያ ቀን ጀምሮ እስከ ዛሬ ድረስ ይህን ለእስራኤል ደንብና ሥርዐት አደረገው።

26. ዳዊት ወደ ጺቅላግ በመጣ ጊዜ፣ ወዳጆቹ ለሆኑት ለይሁዳ ሽማግሌዎች፣ “ከእግዚአብሔር ጠላቶች የተገኘ ስጦታ እነሆ፤” በማለት ከምርኮው ላይ ከፍሎ ላከላቸው።

27. ይህንም፣ በቤቴል፣ በደቡብ ራሞትና በየቲር ለነበሩ፣

28. በኦሮዔር፣ በሢፍሞት፣ በኤሽትሞዓና

29. በራካል እንዲሁም በይረሕምኤላውያንና በቄናውያን ከተሞች ለሚኖሩ፣

30. በሔርማ፣ በቦራሣን፣ በዓታክ፣

31. በኬብሮን እንዲሁም ዳዊትና ሰዎቹ በተዘዋወሩባቸው ስፍራዎች ሁሉ ለነበሩት ላከላቸው።