ምዕራፎች

  1. 1
  2. 2
  3. 3
  4. 4
  5. 5
  6. 6
  7. 7
  8. 8
  9. 9
  10. 10
  11. 11
  12. 12

ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

መክብብ 2 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

ምድራዊ ደስታ ከንቱ ነው

1. እኔም በልቤ፣ “መልካም የሆነውን ለማወቅ፣ በተድላ ደስታ እፈትንሃለሁ” አልሁ፤ ነገር ግን ያም ከንቱ ነበረ።

2. ደግሞም፣ “ሣቅ ሞኝነት ነው፤ ተድላ ደስታስ ምን ይጠቅማል?” አልሁ።

3. አሁንም አእምሮዬ በጥበብ እየመራኝ ራሴን በወይን ጠጅ ደስ ለማሰኘት፣ ሞኝነትንም ለመያዝ ሞከርሁ፤ ሰዎች በአጭር የሕይወት ዘመናቸው ከሰማይ በታች ባለው ላይ ቢሠሩት ሊጠቅማቸው የሚችል ምን እንደሆነ ለማየት ፈለግሁ።

4. ታላላቅ ነገሮችን አከናወንሁ፤ ለራሴ ቤቶችን ሠራሁ፤ ወይንንም ተከልሁ፤

5. አትክልትን ተከልሁ፤ የመዝናኛ ስፍራዎችን አዘጋጀሁ፤ በእነዚህም ላይ ፍሬ የሚያፈሩ የዛፍ ዐይነቶችን ሁሉ ተከልሁባቸው፤

6. የሚለመልሙ ዛፎችን ለቦይ የሚሆኑ የውሃ ማጠራቀሚያዎችን ሠራሁ።

7. ወንድና ሴት ባሪያዎችን ገዛሁ፤ በቤቴም የተወለዱ ሌሎች ባሪያዎች ነበሩኝ። ከእኔ በፊት በኢየሩሳሌም ከነበሩት ይልቅ ብዙ የከብት፣ የበግና የፍየል መንጋዎች ነበሩኝ።

8. ለራሴም ብርንና ወርቅን፣ የነገሥታትና የአውራጃዎችን ሀብት አካበትሁ፤ ወንድና ሴት አዝማሪዎች፣ የሰው መደሰቻ የሆኑ ቅምጦች ነበሩኝ።

9. ከእኔ በፊት በኢየሩሳሌም ከነበሩት ሁሉ ይልቅ እጅግ ታላቅ ሆንሁ፤ በዚህ ሁሉ ጥበቤ ከእኔ ጋር ነበረች።

10. ዐይኔ የፈለገውን ሁሉ አልከለከልሁትም፤ለልቤም ምድራዊ ደስታን አልነፈግሁትም፤ልቤ በሠራሁት ሁሉ ደስ አለው፤ይህም የድካሜ ሁሉ ዋጋ ነበረ።

11. ሆኖም እጆቼ የሠሩትን ሁሉ፣ለማግኘትም የደከምሁትን ድካም ሁሉ ሳስብ፣ሁሉም ከንቱ፣ ነፋስንም እንደ መከተል ነበር፤ከፀሓይ በታች ምንም ትርፍ አልነበረም።

ጥበብና ሞኝነት ከንቱ ናቸው

12. ከዚያም ጥበብን፣እብደትንና ሞኝነትን ለመመርመር ሐሳቤን መለስሁ፤አስቀድሞ ከተደረገው በቀር፣ከንጉሥ በኋላ የሚመጣው ሰው ምን ሊያደርግ ይችላል?

13. ብርሃን ከጨለማ እንደሚበልጥ ሁሉ፣ጥበብም ከሞኝነት እንደሚበልጥ ተመለከትሁ።

14. የጠቢብ ሰው ዐይኖች ያሉት በራሱ ውስጥ ነው፤ሞኝ ግን በጨለማ ውስጥ ይራመዳል፤ሆኖም የሁለቱም ዕድል ፈንታ፣አንድ መሆኑን ተገነዘብሁ።

15. ከዚያም በልቤ፣“የሞኙ ዕድል ፈንታ በእኔም ላይ ይደርሳል፤ታዲያ ጠቢብ በመሆኔ ትርፌ ምንድን ነው?” አልሁ።በልቤም፣“ይህም ደግሞ ከንቱ ነው” አልሁ።

16. ጠቢቡም ሰው እንደ ሞኙ ለዘላለም አይታወስምና፤በሚመጡት ዘመናት ሁለቱም ይረሳሉ።ለካ፣ ጠቢቡምእንደ ሞኙ መሞቱ አይቀርም!

ጥረት ከንቱ ነው

17. ስለዚህ ከፀሓይ በታች የሚሠራው ሥራ አሳዛኝ ስለ ሆነብኝ ሕይወትን ጠላሁ፤ ይህም ሁሉ ከንቱ፣ ነፋስንም እንደ መከተል ነው።

18. ከፀሓይ በታች የደከምሁበትን ነገር ሁሉ ጠላሁት፣ ከኋላዬ ለሚመጣው የግድ እተውለታለሁና።

19. እርሱ ጠቢብ ወይም ሞኝ ይሆን እንደሆነ ማን ያውቃል? ሆኖም ከፀሓይ በታች ድካሜንና ችሎታዬን ባፈሰ ስሁበት ሥራ ሁሉ ላይ ባለቤት ይሆንበታል፤ ይህም ደግሞ ከንቱ ነው።

20. ስለዚህ ከፀሓይ በታች በደከምሁበት ነገር ሁሉ ላይ ልቤ ተስፋ መቊረጥ ጀመረ፤

21. ምክንያቱም ሰው ሥራውን በጥበብ፣ በዕውቀትና በብልኀት ሠርቶ፣ ከዚያ ያለውን ሁሉ ለሌላ ላልለፋበት ሰው ይተውለታል። ይህም ደግሞ ከንቱና ትልቅ ጒዳት ነው።

22. ሰው ከፀሓይ በታች በሚደክምበት ጥረትና ልፋት ሁሉ ትርፉ ምንድን ነው?

23. በዘመኑ ሁሉ ሥራው ሥቃይና ሐዘን ነው፤ በሌሊትም እንኳ ቢሆን አእምሮው አያርፍም። ይህም ደግሞ ከንቱ ነው።

24. ለሰው ከመብላትና ከመጠጣት፣ በሥራውም ከመርካት ሌላ የሚሻለው ነገር የለውም፤ ይህም ደግሞ ከእግዚአብሔር እጅ እንደሚሰጥ አየሁ፤

25. ከእርሱ ዘንድ ካልሆነ ማን መብላትና መደሰት ይችላል?

26. እግዚአብሔር፣ ደስ ለሚያሰኘው ሰው ጥበብን፣ ዕውቀትንና ደስታን ይሰጠዋል። ለኀጢአተኛ ግን፣ እግዚአብሔርን ደስ ለሚያሰኘው ይተውለት ዘንድ፣ ሀብትን የመሰብሰብና የማከናወን ተግባር ይሰጠዋል። ይህም ከንቱ፣ ነፋስንም እንደ መከተል ነው።