ምዕራፎች

  1. 1
  2. 2
  3. 3
  4. 4
  5. 5
  6. 6
  7. 7
  8. 8
  9. 9
  10. 10
  11. 11
  12. 12

ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

መክብብ 1 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

ሁሉም ነገር ከንቱ ነው

1. በኢየሩሳሌም የነገሠው፣ የዳዊት ልጅ፣ የሰባኪው ቃል፤

2. ሰባኪው፣“ከንቱ፣ ከንቱ፣የከንቱ ከንቱ፤ሁሉም ነገር ከንቱ ነው” ይላል።

3. ከፀሓይ በታች ከሚለፋበት ተግባር ሁሉ፣ሰው ምን ትርፍ ያገኛል?

4. ትውልድ ይሄዳል፤ ትውልድ ይመጣል፤ምድር ግን ለዘላለም ጸንታ ትኖራለች።

5. ፀሓይ ትወጣለች፤ ትጠልቃለችም፤ወደምትወጣበትም ለመመለስ ትጣደፋለች።

6. ነፋስ ወደ ደቡብ ይነፍሳል፤ወደ ሰሜንም ይመለሳል፤ዞሮ ዞሮ ይሄዳል፤ዘወትርም ወደ ዑደቱ ይመለሳል።

7. ወንዞች ሁሉ ወደ ባሕር ይፈሳሉ፤ባሕሩ ግን ፈጽሞ አይሞላም፤ወንዞች ወደ መጡበት ስፍራ፣ወደዚያ እንደ ገና ይመለሳሉ።

8. ሰው መናገር ከሚችለው በላይ፣ነገሮች ሁሉ አድካሚ ናቸው፤ዐይን ከማየት አይጠግብም፤ጆሮም በመስማት አይሞላም።

9. የነበረው ነገር እንደ ገና ይሆናል፤የተደረገውም ተመልሶ ይደረጋል፤ከፀሓይ በታች ምንም አዲስ ነገር የለም።

10. ማንም፣ “እነሆ፤ ይህ አዲስ ነገር ነው!”ሊል የሚችለው አንዳች ነገር አለን?ቀድሞውኑ በዚሁ የነበረ ነው፤ከእኛ በፊት የሆነ ነው።

11. የቀድሞ ነገሮች መታሰቢያ የላቸውም፤ወደ ፊት የሚመጡትም ቢሆኑ፣ከእነርሱ በኋላ በሚተኩት፣ አይታወሱም።

ጥበብ ከንቱ ነው

12. እኔ ሰባኪው፣ በኢየሩሳሌም የእስራኤል ንጉሥ ነበርሁ።

13. ከሰማይ በታች የተደረገውን ሁሉ በጥበብ ለማጥናትና ለመመርመር ራሴን አተጋሁ፤ አምላክ በሰዎች ላይ የጫነው እንዴት ያለ ከባድ ሸክም ነው!

14. ከፀሓይ በታች የተደረገውን ነገር ሁሉ አየሁ፤ ሁሉም ከንቱ፣ ነፋስንም እንደ መከተል ነው።

15. የተጣመመው ሊቃና አይችልም፤የሌለም ነገር ሊቈጠር አይችልም።

16. እኔም በልቤ፣ “እነሆ፤ ከእኔ በፊት በኢየሩሳሌም ከገዙት ከማንኛቸውም ይልቅ ታላቅ ሆኛለሁ፤ ጥበብም በዝቶልኛል፤ በብዙ ጥበብና ዕውቀት ተመክሮም ዐልፌአለሁ” አልሁ።

17. ከዚያም የጥበብንና የእብደትን፣ የሞኝነትንም ነገር ለመገንዘብ ራሴን አተጋሁ፤ ይህም ነፋስን እንደ መከተል መሆኑን ተረዳሁ።

18. ጥበብ ሲበዛ፣ ትካዜ ይበዛልና፤ዕውቀት ሲጨምርም ሐዘን ይበዛል።