ምዕራፎች

  1. 1
  2. 2
  3. 3
  4. 4
  5. 5
  6. 6
  7. 7
  8. 8
  9. 9
  10. 10
  11. 11
  12. 12

ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

መክብብ 8 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

1. ነገሮችን መግለጽ የሚችል፣እንደ ጠቢብ ያለ ሰው ማን ነው?ጥበብ የሰውን ፊት ታበራለች፤የከበደ ገጽታውንም ትለውጣለች።

ንጉሥን ታዘዝ

2. በእግዚአብሔር ፊት መሐላ ስለፈጸምህ፣ የንጉሥን ትእዛዝ አክብር እልሃለሁ።

3. ከንጉሥ ፊት ተጣድፈህ አትውጣ፤ የወደደውንም ማድረግ ስለሚችል ለጥፋት አትሰለፍ።

4. የንጉሥ ቃል የበላይ ስለ ሆነ እርሱን፣ “ምን ታደርጋለህ?” ማን ሊለው ይችላል?

5. እርሱን የሚታዘዝ ሁሉ አይጐዳም፤ጥበበኛም ልብ ትክክለኛውን ጊዜና ተገቢውን አሠራር ያውቃል።

6. የሰው መከራ እጅግ ቢጫነውም፣ለሁሉም ነገር ትክክለኛ ጊዜና ተገቢ አሠራር አለው።

7. ሰው የወደ ፊቱን ስለማያውቅ፣ሊመጣ ያለውን ማን ሊነግረው ይችላል?

8. ሰው ነፋስን መቈጣጠር አይችልም፤በዕለተ ሞቱም ላይ ሥልጣን ያለው ማንም የለም፤በጦርነት ጊዜ ማንም ከግዴታ ነጻ እንደማይሆን፣ክፋትም የሚለማመዷትን አትለቃቸውም።

9. ከፀሓይ በታች የተሠራውን ሁሉ በአእምሮዬ መርምሬ፣ ይህን ሁሉ አየሁ። ሰው ሰውን ለመጒዳት ገዥ የሚሆንበት ጊዜ አለ።

10. እንዲሁም ወደ ቅዱሱ ስፍራ ይመጡና ይሄዱ የነበሩት ክፉዎች ተቀብረው አየሁ፤ ይህን ባደረጉበት ከተማም ይመሰገኑ ነበር፤ ይህም ደግሞ ከንቱ ነው።

11. በወንጀል ላይ ባፋጣኝ ፍርድ ካልተሰጠ፣ የሰዎች ልብ ክፉን በማድረግ ዕቅድ ይሞላል።

12. ኀጥእ መቶ ወንጀል ሠርቶ ዕድሜው ቢረዝምም፣ እግዚአብሔርን የሚያከብሩ፣ ፈሪሀ እግዚአብሔር ያላቸው ሰዎች መልካም እንደሚሆንላቸው ዐውቃለሁ።

13. ነገር ግን ክፉዎች እግዚአብሔርን ስለማይፈሩ መልካም አይሆንላቸውም፤ ዕድሜያቸው እንደ ጥላ አይረዝምም።

14. በምድር ላይ የሚከሠት ሌላም ከንቱ ነገር አለ፤ ጻድቃን ለክፉዎች የሚገባውን፣ ክፉ ሰዎችም ለጻድቃን የሚገባውን ይቀበላሉ፤ ይህም ደግሞ ከንቱ ነገር ነው አልሁ።

15. ለሰው፣ ከፀሓይ በታች ከመብላት፣ ከመጠጣትና ከመደሰት ሌላ የተሻለ ነገር ስለሌለ፣ በሕይወት ደስ መሰኘት መልካም ነው አልሁ፤ ስለዚህ እግዚአብሔር ከፀሓይ በታች በሰጠው የሕይወት ዘመኑ ሁሉ በሥራው ደስታ ይኖረዋል።

16. ጥበብን ለማወቅና ሌት ተቀን እንቅልፍ የማያውቀውን በምድር ያለውን የሰውን ድካም ለመገንዘብ በአእምሮዬ ስመረምር፣

17. እግዚአብሔር ያደረገውን ሁሉ አየሁ። ከፀሓይ በታች የሚደረገውን ማንም ሊያውቅ አይችልም፤ ሰው ለመመርመር ብዙ ቢጥርም፣ ትርጒሙን ማግኘት አይችልም፤ ጠቢብም እንኳ ዐውቀዋለሁ ቢል፣ ፈጽሞ ሊገነዘበው አይችልም።