ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ሮሜ 4:1-12 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

1. እንግዲህ በሥጋ የቀድሞ አባታችን የሆነ አብርሃም በዚህ ረገድ ምን አገኘ እንላለን?

2. አብርሃም በሥራ ጸድቆ ቢሆን ኖሮ፣ የሚመካበት ነበረው፤ ነገር ግን በእግዚአብሔር ፊት መመካት አይችልም።

3. መጽሐፍስ ምን ይላል? “አብርሃም እግዚአብሔርን አመነ፤ ጽድቅም ሆኖ ተቈጠረለት።”

4. አንድ ሰው ሥራ ከሠራ ደመወዙ እንደ ስጦታ ሳይሆን እንደ ተገቢ ዋጋው ይቈጠርለታል።

5. ነገር ግን ለማይሠራው፣ ኃጥኡን ሰው ጻድቅ በሚያደርግ በእግዚአብሔር ለሚያምን ሰው፣ እምነቱ ጽድቅ ሆኖ ይቈጠርለታል።

6. ዳዊትም ጽድቅ ያለ ሥራ ስለሚቈጠርለት ሰው ብፅዕና እንዲህ ብሎአል፤

7. “መተላለፋቸው ይቅር የተባለላቸው፣ኀጢአታቸው የተሰረየላቸው፣ብፁዓን ናቸው።

8. ኀጢአቱን፣ ጌታ ከቶ የማይቈጥርበት ሰውብፁዕ ነው።”

9. ይህ ብፅዕና ለተገረዙት ብቻ ነው ወይስ ላልተገረዙትም? የአብርሃም እምነቱ ጽድቅ ሆኖ ተቈጠረለት ብለናል።

10. ታዲያ እንዴት ተቈጠረለት? ከተገረዘ በኋላ ነው ወይስ ከመገረዙ በፊት? የተቈጠረለት ከተገረዘ በኋላ ሳይሆን ከመገረዙ በፊት ነው።

11. ሳይገረዝ በነበረው እምነት ላገኘው ጽድቅ፣ የመገረዝን ምልክት ይኸውም የጽድቅን ማኅተም ተቀበለ፤ ስለዚህ ለሚያምኑ ነገር ግን ላልተገረዙት ጽድቅ ይቈጠርላቸው ዘንድ የሁሉ አባት ነው።

12. እርሱ ለተገረዙትም አባት ነው፤ መገረዝ ብቻ ሳይሆን፣ አባታችን አብርሃም ከመገረዙ በፊት የነበረውን የእምነቱን ፈለግ ለሚከተሉ ሁሉ ነው።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ ሮሜ 4