ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ዘኁልቍ 5:10-27 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

10. የእያንዳንዱ ሰው የተቀደሰ ስጦታ ለካህኑ ይሆናል፤ ለካህኑ የሚሰጠውም ሁሉ የራሱ ይሆናል።’ ”

11. ከዚህ በኋላ እግዚአብሔር (ያህዌ) ሙሴን እንዲህ አለው፤

12. “እስራኤላውያንን ተናገራቸው፤ እንዲህም በላቸው፤ ‘አንዲት ባለ ትዳር ሴት ወደ ሌላ ወንድ በማዘንበል ለባሏ ያላትን ታማኝነት አጒድላ፣

13. ከሌላ ሰው ጋር ብትተኛ፣ ይህም እጅ ከፍንጅ ባለመያዟ ምክንያት ይህ ከባሏ ቢደበቅ፣ የሚመሰክርባት ሰው ባይኖርና መርከሷም ባይገለጥ፣

14. ባሏ የቅናት መንፈስ አድሮበት ቢጠረጥርና በርግጥም ጐድፋ ብትገኝ ወይም ባሏ የቅናት መንፈስ አድሮበት ቢጠረጥርና እርሷ ግን ጐድፋ ባትገኝ፣

15. ወደ ካህኑ ይውሰዳት፤ ስለ እርሷም አንድ ኪሎ ገብስ ዱቄት ለቊርባን ይውሰድ፤ በላዩ ላይ ዘይት አያፍስስበት፤ ዕጣንም አይጨምርበት፤ ይህ ስለ ቅናት የቀረበ የእህል ቊርባን በደልን የሚያሳስብ የመታሰቢያ ቍርባን ነውና።

16. “ ‘ካህኑ ሴትየዋን ያመጣትና በእግዚአብሔር (ያህዌ) ፊት እንድትቆም ያደርጋታል፤

17. ከዚያም የተቀደሰ ውሃ በሸክላ ዕቃ ቀድቶ በማደሪያው ድንኳን ካለው ወለል ጥቂት ዐፈር ቈንጥሮ በውሃው ውስጥ ይጨምራል።

18. ካህኑ ሴትየዋን በእግዚአብሔር (ያህዌ) ፊት እንድትቆም ካደረገ በኋላ የጠጒሯን መሸፈኛ ይገልጣል፤ ስለ ቅናት የቀረበውን የመታሰቢያ ቍርባን በእጇ ያስይዛታል፤ ከዚያም ካህኑ ርግማን የሚያመጣውን መራራ ውሃ በእጁ ይይዛል።

19. ካህኑም ሴትየዋን ያስምላታል፤ እንዲህም ይላታል፤ “ሌላ ወንድ አብሮሽ ካልተኛ በትዳር ላይ ሆነሽ ወደ ርኩሰት ካላዘነበልሽ ይህ ርግማን የሚያመጣ መራራ ውሃ ጒዳት አያድርስብሽ፤

20. ነገር ግን በትዳር ላይ እያለሽ ወደ ርኵሰት በማዘንበል ከባልሽ ሌላ ከወንድ ጋር በመተኛት ከጐደፍሽ”፣

21. እዚህ ላይ ካህኑ እንዲህ በማለት ሴትየዋን በርግማን መሐላ ያስምላታል፤ “እግዚአብሔር (ያህዌ) ጭንሽን እያሰለለና ሆድሽን እያሳበጠ በሕዝብሽ መካከል ርግማንና መሐላ ያድርግብሽ፤

22. ይህን ርግማን የሚያመጣ ውሃ በጠጣሽ ጊዜም ሆድሽን ያሳብጠው፤ ጭንሽን ያሰልለው፤”“ ‘ሴትዮዋም፣ “አሜን፤ አሜን” ትበል።

23. “ ‘ካህኑ እነዚህን መርገሞች በሰሌዳ ላይ ይጻፍ፤ በመራራውም ውሃ ይደምስሳቸው።

24. ርግማን የሚያመጣውንም ውሃ ሴትየዋ እንድትጠጣ ያድርግ፤ ውሃውም ወደ ሰውነቷ ገብቶ የመረረ ሥቃይ ያስከትልባታል።

25. ካህኑ ለቅናት የቀረበውን የእህል ቊርባን ይቀበላት፤ በእግዚአብሔር (ያህዌ) ፊት ወዝውዞ ወደ መሠዊያው ያቅርበው።

26. ካህኑ የመታሰቢያ ቊርባን እንዲሆን እፍኝ የእህል ቍርባን ከዚያ ወስዶ በመሠዊያው ላይ ያቃጥለው፤ ከዚያም በኋላ ሴቲቱ ውሃውን እንድትጠጣ ያድርግ።

27. ራሷን በማጒደፍ ለባሏ ያላትን ታማኝነት አጒድላ ከሆነ፣ ርግማን የሚያመጣውን ውሃ እንድትጠጣ ሲደረግ ውሃው ወደ ሰውነቷ ገብቶ ክፉ ሥቃይ ያመጣባታል፤ ሆዷ ያብጣል፤ ጭኗ ይሰልላል፤ በሕዝቦቿም ዘንድ የተረገመች ትሆናለች።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ ዘኁልቍ 5