ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ዘሌዋውያን 7:12-22 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

12. “ ‘መሥዋዕቱን የሚያቀርበው ለምስጋና መግለጫ ከሆነ፣ ከምስጋና መሥዋዕቱ ጋር ያለ እርሾ የተጋገረና በዘይት የተለወሰ ኅብስት እርሾ ሳይገባበት በሥቡ ተጋግሮ ዘይት የተቀባ ቂጣ በሚገባ ታሽቶ በዘይት የተለወሰም የላመ ዱቄት ኅብስት አብሮ ያቅርብ።

13. ለምስጋና ከሚሆነው የኅብረት መሥዋዕት ጋር በእርሾ የተጋገረ ኅብስት ያቅርብ።

14. ከእያንዳንዱም ዐይነት አንዳንድ አንሥቶ ለእግዚአብሔር (ያህዌ) የተለየ ቊርባን በማድረግ ያቅርብ፤ ይህም የኅብረት መሥዋዕቱን ደም ለሚረጨው ካህን ይሰጥ።

15. ለምስጋና የሚሆነው የኅብረት መሥዋዕት ሥጋ፣ በቀረበበት ዕለት ይበላ እንጂ አንዳች አይደር።

16. “ ‘መሥዋዕቱ ስእለት በመፈጸሙ ወይም በበጎ ፈቃድ የሚቀርብ ከሆነ፣ በቀረበበት ዕለት ይበላ፤ የተረፈውም ሁሉ በማግስቱ ይበላ።

17. እስከ ሦስት ቀን የቆየ ማንኛውም የመሥዋዕቱ ሥጋ ይቃጠል።

18. ማንኛውም የኅብረት መሥዋዕት ሥጋ በሦስተኛው ቀን ከተበላ ተቀባይነት የለውም፤ ርኵስ በመሆኑ ላቀረበው ሰው ዋጋ አይኖረውም፤ ከዚያም የበላ ሰው የበደል ዕዳ ይሆንበታል።

19. “ ‘ርኩስ ከሆነ ነገር ጋር የተነካካ ሥጋ ይቃጠል እንጂ አይበላ። ሌላውን ሥጋ ግን በሥርዐቱ መሠረት ንጹሕ የሆነ ማንኛውም ሰው ይብላ፤

20. ነገር ግን ንጹሕ ያልሆነ ማንኛውም ሰው ለእግዚአብሔር (ያህዌ) የቀረበውን የትኛውንም የኅብረት መሥዋዕት ሥጋ ቢበላ፣ ከሕዝቡ ፈጽሞ ይወገድ።

21. ማንኛውም ሰው የሰውን ርኵሰት ወይም ርኩስ እንስሳን ወይም ማንኛውንም ርኩስ ነገር ቢነካና ለእግዚአብሔር (ያህዌ) ከቀረበው የኅብረት መሥዋዕት ሥጋ ቢበላ፣ ያ ሰው ፈጽሞ ከሕዝቡ ይወገድ።

22. እግዚአብሔር (ያህዌ) ሙሴን እንዲህ አለው፤

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ ዘሌዋውያን 7