ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ዕዝራ 7:1-10 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

1. ከእነዚህም ነገሮች በኋላ በፋርስ ንጉሥ በአርጤክስስ ዘመነ መንግሥት፣ ዕዝራ የሠራያ ልጅ፣ የዓዛርያስ ልጅ፣ የኬልቅያስ ልጅ

2. የሰሎም ልጅ፣ የሳዶቅ ልጅ፣ የአኪጦብ ልጅ፣

3. የአማርያ ልጅ፣ የዓዛርያስ ልጅ፣ የመራዮት ልጅ፣

4. የዘራእያ ልጅ፣ የኦዚ ልጅ፣ የቡቂ ልጅ፣

5. የአቢሱ ልጅ፣ የፊንሐስ ልጅ፣ የአልዓዛር ልጅ፣ የታላቁ ካህን የአሮን ልጅ፣

6. ይህ ዕዝራ ከባቢሎን መጣ። እርሱም የእስራኤል አምላክ እግዚአብሔር ለሙሴ የሰጠውን ሕግ በሚገባ የሚያውቅ የሕግ መምህር ነበር። የአምላኩ የእግዚአብሔር እጅ በእርሱ ላይ ስለ ነበረች፣ የጠየቀውን ሁሉ ንጉሡ ፈቀደለት።

7. እንደዚሁም አንዳንድ እስራኤላውያን፣ ከካህናት፣ ከሌዋውያን፣ ከመዘምራን፣ ከበር ጠባቂዎችና ከቤተ መቅደሱ አገልጋዮች ጋር በመሆን በንጉሡ በአርጤክስስ ዘመነ መንግሥት በሰባተኛው ዓመት ወደ ኢየሩሳሌም መጡ።

8. ዕዝራ በንጉሡ ሰባተኛ ዓመት በአምስተኛው ወር ኢየሩሳሌም ደረሰ።

9. መልካሚቱ የእግዚአብሔር እጅ በእርሱ ላይ ስለ ነበረች፣ ከባቢሎን በመጀመሪያው ወር በመጀመሪያው ቀን ተነሥቶ በአምስተኛው ወር በመጀመሪያው ቀን ኢየሩሳሌም ደረሰ።

10. ዕዝራ የእግዚአብሔርን ሕግ በማጥናትና በማድረግ፣ ለእስራኤልም ሥርዐቱንና ሕጉን በማስተማር ራሱን ፈጽሞ ሰጥቶ ነበር።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ ዕዝራ 7