ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ኤርምያስ 38:8-20 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

8. አቤሜሌክ ከቤተ መንግሥት ወጥቶ ንጉሡን እንዲህ አለው፤

9. “ጌታዬ ንጉሥ ሆይ፤ እነዚህ ሰዎች በነቢዩ በኤርምያስ ላይ ባደረጉት ነገር ሁሉ ክፋትን አድርገዋል፤ ከከተማዪቱም እንጀራ በጠፋ ጊዜ በራብ እንዲሞት ጒድጓድ ውስጥ ጥለውታል።”

10. ንጉሡም ኢትዮጵያዊውን አቤሜሌክን፣ “ሠላሳ ሰዎች ከዚህ ይዘህ ሂድ፤ ነቢዩ ኤርምያስንም ሳይሞት ከጒድጓድ አውጣው” ብሎ አዘዘው።

11. አቤሜሌክም ሰዎቹን ይዞ በቤተ መንግሥቱ ግምጃ ቤት ሥር ወዳለው ክፍል ሄደ፤ ያረጀ ጨርቅና ያለቀ ልብስ ከዚያ ወስዶ ወደ ኤርምያስ ወደ ጒድጓዱ ውስጥ በገመድ አወረደለት።

12. ኢትዮጵያዊው አቤሜሌክ ኤርምያስን፣ “ይህን ያረጀ ጨርቅና ያረጀ ልብስ ገመዱ እንዳይከረክርህ በብብትህ ሥር አድርገው አለው፤ ኤርምያስም እንዲሁ አደረገ፤

13. እነርሱም በገመዱ ጐትተው ከጒድጓዱ አወጡት። ኤርምያስም በዘበኞች አደባባይ ሰነበተ።

14. ንጉሡ ሴዴቅያስ ወደ ነቢዩ ወደ ኤርምያስ ልኮ ወደ እግዚአብሔር ቤተ መቅደስ ሦስተኛው በር አስመጣውና፤ “አንድ ነገር እጠይቅሃለሁ፤ ምንም አትሸሽገኝ” አለው።

15. ኤርምያስም ሴዴቅያስን፣ “መልስ ብሰጥህ አትገድለኝምን? ምክር ብሰጥህ አትሰማኝም” አለው።

16. ንጉሥ ሴዴቅያስ፣ “ለኤርምያስ፣ እስትንፋስ የሰጠ ሕያው እግዚአብሔርን! በእርግጥ አልገድልህም፤ ሕይወትህንም ለሚሿት አሳልፌ አልሰጥም” ብሎ በምስጢር ማለለት።

17. ኤርምያስም ሴዴቅያስን እንዲህ አለው፤ “የእስራኤል አምላክ የሰራዊት ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፤ ‘ለባቢሎን ንጉሥ የጦር መኰንኖች እጅህን ብትሰጥ፣ ሕይወትህ ትተርፋለች፤ ይህችም ከተማ አትቃጠልም፤ አንተና ቤተ ሰብህም በሕይወት ትኖራላችሁ።

18. ለባቢሎን ንጉሥ የጦር መኰንኖች እጅህን ባትሰጥ ግን ይህች ከተማ ለባቢሎናውያን ዐልፋ ትሰጣለች፤ እነርሱም ያቃጥሏታል፤ አንተም ራስህ ከእጃቸው አታመልጥም።’ ”

19. ንጉሡም ሴዴቅያስ ኤርምያስን፣ “ወደ ባቢሎን የኰበለሉት አይሁድ እንዲያላግጡብኝ፣ ባቢሎናውያን ለእነርሱ ዐሳልፈው ይሰጡኛል ብዬ እፈራለሁ” አለው።

20. ኤርምያስም እንዲህ አለው፤ “ዐሳልፈው አይሰጡህም፣ ብቻ የምነግርህን የእግዚአብሔር ቃል ታዘዝ፤ መልካም ይሆንልሃል፤ ሕይወትህም ትተርፋለች።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ ኤርምያስ 38