ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

አስቴር 8:9-14 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

9. ኒሳን በተባለው በሦስተኛው ወር ሃያ ሦስተኛ ቀን የቤተ መንግሥቱ ጸሓፊዎች በአስቸኳይ ተጠርተው ነበር፤ እነርሱም የመርዶክዮስን ትእዛዝ ሁሉ ለአይሁድ፣ እንዲሁም ከህንድ ጀምሮ እስከ ኢትዮጵያ ድረስ፣ በአንድ መቶ ሃያ ሰባት አውራጃዎች ለሚገኙ እንደራሴዎች፣ የአውራጃ ገዦችና መኳንንት ሁሉ ጻፉ። እነዚህም ትእዛዞች የተጻፉት በእያንዳንዱ አውራጃ ፊደልና በእያንዳንዱ ሕዝብ ቋንቋ፣ እንደዚሁም ለአይሁድ በገዛ ፊደላቸውና በገዛ ቋንቋቸው ነበር።

10. መርዶክዮስ ትእዛዙን በንጉሥ ጠረክሲስ ስም ጽፎ በንጉሡ የቀለበት ማኅተም አተመው፤ ከዚያም በተለይ ለንጉሡ በተገሩ ፈጣን ፈረሶች በሚጋልቡ መልእክተኞች እጅ ላከው።

11. የንጉሡም ዐዋጅ በየከተማው የሚኖሩ አይሁድ ሁሉ እንዲሰበሰቡና ራሳቸውን ከጥቃት እንዲከላከሉ እንዲሁም በራሳቸው፣ በሚስቶቻቸውና በልጆቻቸው ላይ አደጋ የሚያደርስባቸውን የየትኛውንም ዜጋ ወይም አውራጃ የታጠቀ ኀይል እንዲያጠፉ፣ እንዲገድሉ፣ እንዲደመስሱና የጠላቶቻቸውን ሀብት እንዲዘርፉ ፈቀደላቸው።

12. አይሁድ በመላው የንጉሥ ጠረክሲስ አውራጃ ሁሉ ይህን እንዲፈጽሙ የተወሰነው አዳር በተባለው በዐሥራ ሁለተኛው ወር ዐሥራ ሦስተኛ ቀን ነበር።

13. አይሁድ በዚያን ቀን ጠላቶቻቸውን ለመበቀል ዝግጁ እንዲሆኑ፣ የዋናው ዐዋጅ ቅጅ ሕግ ወደየአውራጃው እንዲላክና የየአገሩም ሕዝብ እንዲያውቀው ተደረገ።

14. በቤተ መንግሥቱ ፈረሶች የተቀመጡ መልእክተኞችም፣ በንጉሡ አስቸኳይ ትእዛዝ ጋልበው ወጡ፤ ዐዋጁም በሱሳ ግንብ ተነገረ።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ አስቴር 8