ምዕራፎች

  1. 1
  2. 2
  3. 3
  4. 4
  5. 5
  6. 6
  7. 7
  8. 8
  9. 9
  10. 10

ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

አስቴር 8 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

ንጉሡ በአይሁድ ስም የተናገረው ዐዋጅ

1. በዚያኑ ዕለት ንጉሥ ጠረክሲስ የአይሁድን ጠላት የሐማን ቤት ንብረት ለንግሥት አስቴር ሰጣት፤ አስቴርም መርዶክዮስ እንዴት እንደሚዛመዳት ለንጉሡ ነግራው ስለ ነበር፣ መርዶክዮስ ወደ ንጉሡ ዘንድ ቀረበ።

2. ንጉሡ ከሐማ መልሶ የወሰደውን ባለ ማኅተም ቀለበት አውልቆ ለመርዶክዮስ ሰጠው፤ አስቴርም መርዶክዮስን በሐማ ቤት ንብረት ላይ ሾመችው።

3. አስቴር በንጉሡ እግር ላይ ወድቃ በማልቀስ ልመናዋን እንደ ገና አቀረበች። አጋጋዊው ሐማ በአይሁድ ላይ የሸረበው ክፉ ሤራ እንዲሽር ለመነችው።

4. ከዚያም ንጉሡ የወርቅ ዘንጉን ለአስቴር ዘረጋላት፤ እርሷም ተነሥታ በፊቱ ቆመች።

5. እንዲህም አለች፤ “ንጉሡን ደስ የሚያሰኘውና እኔም በፊቱ ሞገስ አግኝቼ ከሆነ፣ ጉዳዩም በንጉሡ ዘንድ ተገቢ ሆኖ ከተገኘና በእኔም ደስ ከተሰኘ፣ የአጋጋዊው የሐመዳቱ ልጅ ሐማ በንጉሡ አውራጃዎች ሁሉ የሚገኙትን አይሁድ ለማጥፋት የሸረበውን ሤራና የጻፈውን ደብዳቤ የሚሽር ትእዛዝ ይጻፍ።

6. በሕዝቤ ላይ መዐት ሲወርድ እያየሁ እንዴት ልታገሥ እችላለሁ? የቤተ ሰቤንስ መጥፋት እያየሁ እንዴት መቋቋም እችላለሁ?”

7. ንጉሥ ጠረክሲስም ለንግሥት አስቴርና ለአይሁዳዊው ለመርዶክዮስ እንዲህ ሲል መለሰላቸው፤ “እነሆ ሐማ አይሁድን ለማጥፋት ስላቀደ፣ ቤት ንብረቱን ለአስቴር ሰጥቻለሁ፤ እርሱንም በዕንጨት ላይ ሰቅለውታል።

8. በንጉሥ ስም የተጻፈናበቀ ለበቱ የታተመ ደብዳቤ ሊሻር ስለማይችል፣ እናንተ ደግሞ አይሁድን በተመለከተ መልካም መስሎ የታያችሁን ሌላ ዐዋጅ በንጉሡ ስም ጽፋችሁ በንጉሡ የቀለበት ማኅተም አትሙት።”

9. ኒሳን በተባለው በሦስተኛው ወር ሃያ ሦስተኛ ቀን የቤተ መንግሥቱ ጸሓፊዎች በአስቸኳይ ተጠርተው ነበር፤ እነርሱም የመርዶክዮስን ትእዛዝ ሁሉ ለአይሁድ፣ እንዲሁም ከህንድ ጀምሮ እስከ ኢትዮጵያ ድረስ፣ በአንድ መቶ ሃያ ሰባት አውራጃዎች ለሚገኙ እንደራሴዎች፣ የአውራጃ ገዦችና መኳንንት ሁሉ ጻፉ። እነዚህም ትእዛዞች የተጻፉት በእያንዳንዱ አውራጃ ፊደልና በእያንዳንዱ ሕዝብ ቋንቋ፣ እንደዚሁም ለአይሁድ በገዛ ፊደላቸውና በገዛ ቋንቋቸው ነበር።

10. መርዶክዮስ ትእዛዙን በንጉሥ ጠረክሲስ ስም ጽፎ በንጉሡ የቀለበት ማኅተም አተመው፤ ከዚያም በተለይ ለንጉሡ በተገሩ ፈጣን ፈረሶች በሚጋልቡ መልእክተኞች እጅ ላከው።

11. የንጉሡም ዐዋጅ በየከተማው የሚኖሩ አይሁድ ሁሉ እንዲሰበሰቡና ራሳቸውን ከጥቃት እንዲከላከሉ እንዲሁም በራሳቸው፣ በሚስቶቻቸውና በልጆቻቸው ላይ አደጋ የሚያደርስባቸውን የየትኛውንም ዜጋ ወይም አውራጃ የታጠቀ ኀይል እንዲያጠፉ፣ እንዲገድሉ፣ እንዲደመስሱና የጠላቶቻቸውን ሀብት እንዲዘርፉ ፈቀደላቸው።

12. አይሁድ በመላው የንጉሥ ጠረክሲስ አውራጃ ሁሉ ይህን እንዲፈጽሙ የተወሰነው አዳር በተባለው በዐሥራ ሁለተኛው ወር ዐሥራ ሦስተኛ ቀን ነበር።

13. አይሁድ በዚያን ቀን ጠላቶቻቸውን ለመበቀል ዝግጁ እንዲሆኑ፣ የዋናው ዐዋጅ ቅጅ ሕግ ወደየአውራጃው እንዲላክና የየአገሩም ሕዝብ እንዲያውቀው ተደረገ።

14. በቤተ መንግሥቱ ፈረሶች የተቀመጡ መልእክተኞችም፣ በንጉሡ አስቸኳይ ትእዛዝ ጋልበው ወጡ፤ ዐዋጁም በሱሳ ግንብ ተነገረ።

15. መርዶክዮስ ሰማያዊና ነጭ የቤተ መንግሥት ልብስ ለብሶ፣ ትልቅ የወርቅ አክሊል ደፍቶ፣ ከቀጭን በፍታና ከሐምራዊ ግምጃ የተሠራ መጐናጸፊያ ተጐናጽፎ ከንጉሡ ፊት ወጣ፤ የሱሳ ከተማም ደስታ የተሞላበት በዓል አከበረች።

16. ጊዜውም ለአይሁድ የደስታና የፈንጠዝያ፣ የተድላና የክብር ወቅት ሆነላቸው።

17. የንጉሡ ዐዋጅ በደረሰበት በእያንዳንዱ አውራጃና በእያንዳንዱ ከተማ አይሁድ ደስ አላቸው፤ ሐሤት አደረጉ፤ የፈንጠዝያና የደስታም ቀን ሆነላቸው። አይሁድን ከመፍራታቸው የተነሣ፣ ከሌሎች አገር ዜጎች ብዙ ሕዝብ አይሁድ ሆኑ።