ምዕራፎች

  1. 1
  2. 2
  3. 3
  4. 4
  5. 5

ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ሰቆቃወ 3 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

1. በቊጣው በትር፣መከራ ያየ ሰው እኔ ነኝ።

2. ከፊቱ አስወጣኝ፤በብርሃን ሳይሆን በጨለማ እንድሄድ አደረገኝ።

3. በእርግጥ ቀኑን ሁሉ በመደጋገም፣እጁን በላዬ ላይ መለሰ።

4. እርሱ ሥጋዬንና ቈዳዬን አስረጀ፤ዐጥንቶቼንም ሰባበረ።

5. በምሬትና በድካም፣ቅጥር ሠራብኝ፤ ዙሪያዬንም ከበበኝ።

6. ከሞቱ ብዙ ጊዜ እንደሆናቸው፣በጨለማ እንድኖር አደረገኝ።

7. በቅጥር ውስጥ ዘጋብኝ፤ ስለዚህ ማምለጥ አልቻልሁም፤የእስር ሰንሰለቴንም አከበደብኝ።

8. ርዳታ ፈልጌ ብጣራና ብጮኽ እንኳ፣ጸሎቴን መስማት አልፈለገም።

9. መንገዴን በተጠረቡ ድንጋዮች ዘጋ፤ጐዳናዬንም አጣመመ።

10. አሸምቆ እንደ ተኛ ድብ፣እንደ አደባም አንበሳ፣

11. ከመንገድ ጐትቶ አስወጣኝ፤ ቈራረጠኝም፤ያለ ረዳትም ተወኝ።

12. ቀስቱን ገተረ፤ለፍላጻዎቹም ዒላማ አደረገኝ።

13. ፍላጻዎችን ከሰገባው አውጥቶ፣ልቤን ወጋው።

14. ለሕዝቤ ሁሉ ማላገጫ ሆንሁኝ፤ቀኑን ሙሉ በመሣለቅ ያዜሙብኛል።

15. መራራ ሥር አበላኝ፤ሐሞትም አጠገበኝ።

16. ጥርሴን በድንጋይ ሰበረ፤በትቢያ ውስጥ ረጋገጠኝ።

17. ነፍሴ ሰላምን አጣች፤ደስታ ምን እንደሆነ ረሳሁ።

18. ስለዚህ፣ “ክብሬ፣ ከእግዚአብሔርም ተስፋ ያደረግሁት ሁሉ ሄዶአል” አልሁ።

19. የጭንቀቴንና የመንከራተቴን፣ምሬትንና ሐሞትን አስባለሁ።

20. ዘወትር አስበዋለሁ፤ነፍሴም በውስጤ ተዋርዳለች።

21. ሆኖም ይህን አስባለሁእንግዲያስ ተስፋ አለኝ፤

22. ያልጠፋነው ከእግዚአብሔር ታላቅ ፍቅር የተነሣ ነው፤ርኅራኄው አያልቅምና።

23. ማለዳ ማለዳ አዲስ ነው፤ታማኝነትህም ብዙ ነው።

24. ራሴን እንዲህ አልሁት፤ “እግዚአብሔር ዕድል ፈንታዬ ነው፤ስለዚህ ተስፋ አደርገዋለሁ።

25. እርሱን ተስፋ ለሚያደርጉት፣ለሚፈልገውም ሰው እግዚአብሔር መልካም ነው።

26. ሰው የእግዚአብሔርን ማዳን፣ዝም ብሎ ተስፋ ቢያደርግ መልካም ነው።

27. ሰው በወጣትነቱ፣ቀንበር ቢሸከም መልካም ነው።

28. ብቻውን ዝም ብሎ ይቀመጥ፤ እግዚአብሔር አሸክሞታልና።

29. ፊቱን በዐቧራ ውስጥ ይቅበር፤ተስፋ ሊኖር ይችላልና።

30. ጒንጩን ለሚመታው ሰው ይስጥ፤ውርደትንም ይጥገብ።

31. እግዚአብሔር ሰውን፣ለዘላለም አይጥልምና፤

32. መከራን ቢያመጣ እንኳ ይራራል፤ታላቅ ፍቅሩ አይለወጥምና

33. ሆን ብሎ ችግርን፣ወይም መከራን በሰው ልጆች ላይ አያመጣምና።

34. የምድሪቱ እስረኞች ሁሉ፣በእግር ሲረገጡ፣

35. በልዑል ፊት፣ሰው መብቱ ሲነፈገው፣

36. ሰው ፍትሕ ሲጓደልበት፣ጌታ እንዲህ ዐይነቱን ነገር አያይምን?

37. እግዚአብሔር ካላዘዘ በቀር፤ተናግሮ መፈጸም የሚችል ማን ነው?

38. ክፉም ሆነ መልካም ነገር፣ከልዑል አፍ የሚወጣ አይደለምን?

39. ታዲያ ሕያው ሰው በኀጢአቱ ሲቀጣ፣ስለ ምን ያጒረመርማል?

40. መንገዳችንን እንመርምር፤ እንፈትን፤ወደ እግዚአብሔርም እንመለስ።

41. ልባችንን ከእጃችን ጋር በሰማይ ወዳለው ወደ አምላካችንእናንሣ፤ እንዲህም እንበል፤

42. “ዐምፀናል፤ ኀጢአትም ሠርተናል፤አንተም ይቅር አላልኸንም።

43. “ራስህን በቊጣ ከደንህ፤ አሳደድኸንም፤ያለ ርኅራኄም ገደልኸን።

44. ጸሎት እንዳያልፍ፣ራስህን በደመና ሸፈንህ።

45. በአሕዛብ መካከል፣አተላና ጥራጊ አደረግኸን።

46. “ጠላቶቻችን ሁሉ፣አፋቸውን በእኛ ላይ ከፈቱ።

47. በጥፋትና በመፈራረስ፣በችግርና በሽብር ተሠቃየን።

48. የእንባ ጐርፍ ከዐይኔ ፈሰሰ፤ሕዝቤ አልቋልና።

49. ያለ ዕረፍት፣ያለ ማቋረጥ ዐይኖቼ እንባ ያፈሳሉ፤

50. እግዚአብሔር ከላይ፣ከሰማይ እስኪያይ ድረስ።

51. በከተማዬ ባሉት ሴቶች ሁሉ ላይ የደረሰውን ማየቴ፣ነፍሴን አስጨነቃት።

52. ያለ ምክንያት ጠላቶቼ የሆኑ፣እንደ ወፍ አደኑኝ።

53. ሕይወቴን በጒድጓድ ውስጥ ሊያጠፉ ሞከሩ፣ድንጋይም በላዬ አደረጉ።

54. ውሃ ሞልቶ በዐናቴ ላይ ፈሰሰ፤ጠፍቻለሁ ብዬ አሰብሁ።

55. በጥልቁ ጒድጓድ ውስጥ ሳለሁ፣ እግዚአብሔር ሆይ፤ የአንተን ስም ጠራሁ።

56. ልመናዬን ሰምተሃል፤ “ርዳታም ፈልጌ ስጮኽ፣ከመስማት ጆሮህን አትከልክል።”

57. በጠራሁህ ጊዜ ቀረብኸኝ፣እንዲሁም፣ “አትፍራ” አልኸኝ።

58. ጌታ ሆይ፤ ለእኔ ተሟገትኽልኝ፤ሕይወቴንም ተቤዠህ።

59. እግዚአብሔር ሆይ፤ በእኔ ላይ የተደረገውን ግፍ አየህ፤ፍርዴን ፍረድልኝ!

60. በቀላቸውን ሁሉ፣በእኔም ላይ ያሰቡትን ዐድማ አየህ።

61. እግዚአብሔር ሆይ፤ ስድባቸውን ሁሉ፣በእኔ ላይ ያሰቡትን ዐድማ ሁሉ ሰማህ፤

62. ይህም ቀኑን ሙሉ በእኔ ላይ፣ጠላቶቼ የሚያውጠነጥኑትና የሚያንሾካሹኩት ነው።

63. ተመልከታቸው! ቆመውም ሆነ ተቀምጠው፣በዘፈናቸው ይሣለቁብኛል።

64. እግዚአብሔር ሆይ፤ እጆቻቸው ላደረጉት፣የሚገባውን መልሰህ ክፈላቸው።

65. በልባቸው ላይ መጋረጃን ዘርጋ፤ርግማንህም በላያቸው ይሁን!