ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

መዝሙር 55:1-14 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

1. እግዚአብሔር ሆይ፤ ጸሎቴን ስማ፤ልመናዬን ቸል አትበል፤

2. ወደ እኔ ተመልከት፤ መልስልኝም።በውስጤ ታውኬአለሁ፤ ተናውጬአለሁም፤

3. በጠላት ድምፅ ተሸበርሁ፤በክፉዎች ድንፋታ ደነገጥሁ፤መከራ አምጥተውብኛልና፤በቍጣም ተነሣሥተው ጠላት ሆነውብኛል።

4. ልቤ በውስጤ ተጨነቀብኝ፤የሞት ድንጋጤም በላዬ መጣ።

5. ፍርሀትና እንቅጥቃጤ መጣብኝ፤ሽብርም ዋጠኝ።

6. እኔም እንዲህ አልሁ፤ “ምነው የርግብ ክንፍ በኖረኝ!በርሬ በሄድሁና ባረፍሁ ነበር፤

7. እነሆ፤ ኰብልዬ በራቅሁ፣በምድረ በዳም በሰነበትሁ ነበር፤ ሴላ

8. ከዐውሎ ነፋስና ከውሽንፍር ሸሽቼ፣ወደ መጠለያዬ ፈጥኜ በደረስሁ ነበር።”

9. ጌታ ሆይ፤ ግፍንና ሁከትን በከተማዪቱ ውስጥ አይቼአለሁና፣ግራ አጋባቸው፤ ቋንቋቸውንም ደበላልቅ።

10. ቀንና ሌሊት ቅጥሯ ላይ ወጥተው ይዞሯታል፤ተንኰልና መከራ በውስጧ አለ።

11. ጥፋት በመካከሏ ይገኛል፤ግፍና አታላይነትም ከጎዳናዋ አይጠፋም።

12. የሚዘልፈኝ ጠላት አይደለምና፤ቢሆንማ ኖሮ በታገሥሁት ነበር፤የሚጠላኝ፣ ራሱንም ቀና ቀና ያደረገብኝ ባላንጣ አይደለም፤ቢሆንማ ከእርሱ በተሸሸግሁ ነበር።

13. ነገር ግን አድራጊው አንተ ነህ፤ እኩያዬ፣ ባልንጀራዬና ወዳጄ፤

14. በእግዚአብሔርም ቤት አብረን በሕዝብ መካከል ተመላለስን፤ደስ የሚል ፍቅር በአንድነት ነበረን።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ መዝሙር 55