ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ሕዝቅኤል 47:6-12 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

6. እርሱም፣ “የሰው ልጅ ሆይ፤ ይህን ታየዋለህን?” ሲል ጠየቀኝ።ከዚያም መልሶ ወደ ወንዙ ዳር መራኝ፤

7. እዚያም በደረስሁ ጊዜ፣ በወንዙ ግራና ቀኝ ብዙ ዛፍ አየሁ።

8. እርሱም እንዲህ አለኝ፤ “ይህ ውሃ ወደ ምሥራቅ ምድር ይፈሳል፤ ወደ ባሕሩ ወደሚገባበት ወደ ዓረባ ይወርዳል፤ ወደ ባሕሩም ሲፈስ፣ በዚያ የነበረው ውሃ ንጹሕ ይሆናል።

9. ወንዙ በሚፈስበት ስፍራ ሁሉ ብዙ ሕያዋን ፍጡራን ይኖራሉ። ይህ ውሃ በዚያ ስለሚፈስና ጨውማ የሆነውን ውሃ ንጹሕ ስለሚያደርገው፣ ዓሣ በብዛት ይኖራል፤ ስለዚህ ወንዙ በሚፈስበት ስፍራ ሁሉ ማንኛውም ነገር በሕይወት ይኖራል።

10. ዓሣ አጥማጆች በወንዙ ዳር ይቆማሉ፤ ከዓይንጋዲ እስከ ዓይንኤግላይም ድረስ ያለው ቦታ መረብ መዘርጊያ ይሆናል፤ ዓሣውም እንደ ታላቁ ባሕር ዓሣ፣ የተለያየ ዐይነት ይሆናል።

11. ነገር ግን ረግረጉና ዕቋሪው ውሃ ንጹሕ አይሆንም፤ ጨው እንደሆነ ይቀራል።

12. በወንዙም ዳርና ዳር፣ ፍሬ የሚያፈሩ የዛፍ ዐይነቶች ሁሉ ይበቅላሉ፤ ቅጠላቸው አይደርቅም፤ ፍሬ አልባም አይሆኑም። ከመቅደሱ የሚወጣው ውሃ ስለሚፈስላቸው በየወሩ ያፈራሉ፤ ፍሬያቸው ለምግብ፣ ቅጠላቸውም ለፈውስ ይሆናል።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ ሕዝቅኤል 47