ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

2 ዜና መዋዕል 34:17-32 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

17. በእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ የነበረውንም ገንዘብ አውጥተው ለተቈጣጣሪዎቹና ለሠራተኞቹ አስረክበዋል።”

18. ከዚያም ጸሓፊው ሳፋን ንጉሡን፣ “ካህኑ ኬልቅያስ መጽሐፍ ሰጥቶኛል” አለው። ሳፋንም መጽሐፉን ለንጉሡ አነበበለት።

19. ንጉሡም የሕጉን ቃል በሰማ ጊዜ ልብሱን ቀደደ።

20. እርሱም ለኬልቅያስ፣ ለሳፋን ልጅ ለአኪቃም፣ ለሚክያስ ልጅ ለዓብዶን፣ ለጸሓፊው ለሳፋንና ለንጉሡ የቅርብ አገልጋይ ለዓሳያ ይህን ትእዛዝ ሰጠ፤

21. “ሄዳችሁ ስለ እኔ እንደዚሁም በእስራኤልና በይሁዳ ስላሉት ቅሬታዎች በተገኘው መጽሓፍ ውስጥ ስለ ተጻፈው ነገር እግዚአብሔርን ጠይቁ። አባቶቻችን የእግዚአብሔርን ቃል ስላልጠበቁ በላያችን ላይ ታላቅ የእግዚአብሔር ቊጣ ፈስሶአል፤ በዚህ መጽሐፍ በተጻፈው መሠረት አልተመላለሱምና።”

22. ኬልቅያስና ንጉሡ ከእርሱ ጋር የላካቸው ሰዎች የአልባሳት ጠባቂ የነበረው የሐስራ ልጅ፣ የቲቁዋ ልጅ የሴሌም ሚስት ወደሆነችው ወደ ነቢይቱ ወደ ሕልዳና ሄደው ነገሯት። እርሷም በኢየሩሳሌም ውስጥ በሁለተኛው ክፍለ ከተማ ትኖር ነበር።

23. ነቢይቱም እንዲህ አለቻቸው፤ “የእስራኤል አምላክ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፤ ወደ እኔ ለላካችሁ ሰው እንዲህ ብላችሁ ንገሩት፤

24. ‘እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፤ በይሁዳ ንጉሥ ፊት በተነበበው መጽሐፍ በተጻፈው ርግማን ሁሉ መሠረት፣ በዚህ ስፍራና በሕዝቡ ላይ ጥፋትን አመጣለሁ።

25. እኔን ትተውኝ ለሌሎች አማልክት ዕጣን ስላጠኑና እጃቸው በሠራው ነገር ሁሉ ለቊጣ ስላነሣሡኝ፣ ቊጣዬ በዚህ ስፍራ ይነድ ዳል፤ አይጠፋምም።’

26. እግዚአብሔርን ለመጠየቅ የላካችሁን የይሁዳን ንጉሥ እንዲህ በሉት፤ ‘ስለ ሰማኸው ቃል የእስራኤል አምላክ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፤

27. በዚህ ስፍራና በሕዝቡ ላይ የተናገረውን በሰማህ ጊዜ፣ ልብህ ስለ ተነካና በእግዚአብሔርም ፊት ራስህን ስለአዋረድህ፣ እንዲሁም በእኔ ፊት ራስህን ዝቅ ስላደረግህ፣ ልብስህንም በመቅደድ በፊቴ ስለአለቀስህ፣ ሰምቼሃለሁ ይላል እግዚአብሔር።

28. እነሆ፤ ወደ አባቶችህ እሰበስብሃለሁ፤ በሰላምም ትቀበራለህ፤ በዚህ ቦታና በነዋሪዎቹ ላይ የማመጣውን መከራ ሁሉ በዓይንህ አታይም።’ ” መልሷንም ይዘው ወደ ንጉሡ ሄዱ።

29. ከዚያም ንጉሡ የይሁዳንና የኢየሩሳሌምን ሽማግሌዎች ሁሉ በአንድ ላይ ሰበሰበ።

30. እርሱም ከትንሽ እስከ ትልቅ ካሉት ከይሁዳ ሰዎች፣ ከኢየሩሳሌም ሕዝብ፣ ከካህናትና ከሌዋውያን ጋር ወደ እግዚአብሔር ቤተ መቅደስ ወጣ። በእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ የተገኘውንም የኪዳኑን መጽሐፍ ቃል ሁሉ ለሕዝቡ አነበበላቸው

31. ንጉሡም በዐምዱ አጠገብ ቆሞ፣ እግዚአብሔርን ይከተል ዘንድ በፍጹም ልቡና በፍጹም ነፍሱ ትእዛዛቱን፣ ሕግጋቱንና ሥርዐቱን ለመጠበቅ፣ በዚህ መጽሐፍ ለተጻፈውም የኪዳን ቃል ለመታዘዝ በእግዚአብሔር ፊት ኪዳኑን አደሰ።

32. ከዚህ በኋላ በኢየሩሳሌምና በብንያም የሚኖረው ሁሉ በዚህ ነገር ቃል እንዲገባ አደረገ፤ የኢየሩሳሌምም ሕዝብ የአባቶቹ አምላክ ባዘዘው የአምላክ ቃል ኪዳን መሠረት ፈጸሙ።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ 2 ዜና መዋዕል 34