ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

2 ዜና መዋዕል 18:1-10 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

1. ኢዮሣፍጥ ታላቅ ሀብትና ክብር ባገኘ ጊዜ ከአክዓብ ጋር በጋብቻ ተሳሰረ።

2. ከጥቂት ዓመታት በኋላም አክዓብን ሊጎበኝ ወደ ሰማርያ ወረደ። አክዓብም ለእርሱና አብሮት ለነበረው ሕዝብ ብዙ በግና በሬ ዐረደ፤ ከዚያም በሬማት ዘገለዓድ ላይ አደጋ እንዲጥል አግባባው።

3. የእስራኤል ንጉሥ አክዓብም የይሁዳን ንጉሥ ኢዮሣፍጥን፣ “ሬማት ዘገለዓድን ለመውጋት አብረኸኝ ትሄዳለህን?” ሲል ጠየቀው። ኢዮሣፍጥም፣ “እኔ እንደ አንተው ነኝ፤ ሕዝቤም እንደ ሕዝብህ ነው፤ በጦርነቱ አብረናችሁ እንሰለፋለን” ሲል መለሰለት።

4. ደግሞም ኢዮሣፍጥ የእስራኤልን ንጉሥ፣ “አስቀድመህ ግን የእግዚአብሔርን ፈቃድ ጠይቅ” አለው።

5. ስለዚህ የእስራኤል ንጉሥ አራት መቶ ነቢያትን በአንድነት ሰብስቦ፣ “ሬማት ዘገለዓድን ለመውጋት ልሂድን ወይስ ልቅር?” ሲል ጠየቃቸው።እነርሱም፣ “እግዚአብሔር በንጉሡ እጅ አሳልፎ ይሰጣታልና ሂድ” ብለው መለሱለት።

6. ኢዮሣፍጥ ግን፣ “እንጠይቀው ዘንድ ሌላ የእግዚአብሔር ነቢይ እዚህ የለምን?” አለ።

7. የእስራኤልም ንጉሥ ለኢዮሣፍጥ፣ “መኖሩንማ በእርሱ አማካይነት የእግዚአብሔርን ፈቃድ የምንጠይቅበት አንድ ሰው አሁንም አለ፤ ነገር ግን ምንጊዜም ቢሆን ስለ እኔ ክፉ እንጂ ደግ ትንቢት ስለማይናገር እጠላዋለሁ፤ እርሱም የይምላ ልጅ ሚካያ ነው” ሲል መለሰ።ኢዮሳፍጥም፣ “ንጉሥ እንዲህ ማለት አይገባውም” አለው።

8. የእስራኤልም ንጉሥ ከሹማምቱ አንዱን ጠርቶ “ሂድና የይምላን ልጅ ሚካያን በፍጥነት አምጣው” አለው።

9. የእስራኤል ንጉሥና የይሁዳ ንጉሥ ኢዮሣፍጥ ልብሰ መንግሥታቸውን ለብሰው፣ በሰማርያ ቅጥር በር መግቢያ አጠገብ ባለው ዐውድማ ላይ በየዙፋናቸው ተቀምጠው፣ ነቢያቱ ሁሉ በፊታቸው ትንቢት ይናገሩ ነበር።

10. የክንዓና ልጅ ሴዴቅያስም የብረት ቀንዶች ሠርቶ፣ “እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፤ ‘ሶርያውያን እስኪጠፉ ድረስ በእነዚህ ትወጋቸዋለህ” አለ።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ 2 ዜና መዋዕል 18