ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

2 ነገሥት 4:25-39 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

25. ስለዚህ ተነሥታ የእግዚአብሔር ሰው ወዳለበት ወደ ቀርሜሎስ ተራራ ሄደች።የእግዚአብሔር ሰው በሩቁ ሲያያት አገልጋዩን ግያዝን እንዲህ አለው፤ “ሱነማዪቱን አየሃት፤ ያቻትና!

26. በል ሩጠህ ሂድና፣ ምነው ደኅና አይደለሽምን? ባልሽ ደኅና አይደለምን? ልጅሽስ ደህና አይደለምን? ብለህ ጠይቃት።”እርሷ፣ “ሁሉ ነገር ደህና ነው” አለች።

27. የእግዚአብሔር ሰው ወዳለበት ተራራ ስትደርስም እግሩ ላይ ተጠመጠመች፤ ግያዝ ሊያስለቅቃት ሲመጣ፣ የእግዚአብሔር ሰው ግን፣ “እጅግ አዝናለችና ተዋት! እግዚአብሔር ይህን ለምን ከእኔ እንደሰወረውና እንዳልነገረኝ አልገባኝም” አለ።

28. እርሷም፣ “ጌታዬ፤ ለመሆኑ እኔ ልጅ እንድትሰጠኝ ጠይቄህ ነበርን? ‘አጒል ተስፋ እንዳትሰጠኝ’ አላልሁህምን?” አለችው።

29. ኤልሳዕም ግያዝን፣ “እንግዲህ ወገብህን ታጠቅ፤ በትሬን ያዝና ሩጥ፤ መንገድ ላይ ሰው ብታገኝ ሰላም አትበል፤ ማንም ሰው ሰላም ቢልህ መልስ አትስጥ፤ በትሬንም በልጁ ፊት ላይ አድርግ” አለው።

30. የልጁ እናት ግን፣ “ሕያው እግዚአብሔርን፤ በሕያው ነፍስህም እምላለሁ፣ ፈጽሞ ትቼህ አልሄድም” አለችው፤ ስለዚህ ተነሥቶ ተከተላት።

31. ግያዝም ቀድሞአቸው ሄዶ በትሩን በልጁ ፊት ላይ አደረገ፤ ነገር ግን ድምፅም፣ ምላሽም አልነበረም። ስለዚህ ግያዝ ወደ ኤልሳዕ ተመልሶ፣ “ልጁ አልነቃም” አለው።

32. ኤልሳዕ ወደ ቤት ሲገባም ልጁ ሞቶ በዐልጋው ላይ ተጋድሞ ነበር።

33. ወደ ውስጥም ገባ፤ ከዚያም በሩን በራሱና በልጁ ላይ ዘግቶ ወደ እግዚአብሔር ጸለየ።

34. በዐልጋው ላይ ወጥቶም በልጁ ላይ ተጋደመና አፉን በአፉ፣ ዐይኑን በዐይኑ፣ እጁን በእጁ ላይ አደረገ። ሙሉ በሙሉ እንደተ ዘረጋበትም፣ የልጁ ሰውነት መሞቅ ጀመረ።

35. ኤልሳዕም ተነሥቶ በቤቱ ውስጥ ወዲያና ወዲህ ከሄደ በኋላ ወደ ዐልጋው ወጥቶ እንደ ገና በልጁ ላይ ሙሉ ለሙሉ ተዘረጋበት፤ ልጁም ሰባት ጊዜ አስነጠሰውና ዐይኖቹን ከፈተ።

36. ኤልሳዕም ግያዝን ጠርቶ፣ “ሱነማዪቱን ጥራት፤” አለው፤ እርሱም ጠራት። እንደ መጣችም፣ “በይ ልጅሽን ውሰጂ” አላት።

37. እርሷም ገብታ በእግሩ ላይ ወደቀች፤ በምድርም ላይ ተደፋች፤ ልጇንም ይዛ ወጣች።

38. ኤልሳዕ ወደ ጌልገላ ተመለሰ፤ በዚያም አገር ራብ ነበረ። የነቢያት ማኅበር በፊቱ ተቀምጠው ሳለ አገልጋዩን፣ “ትልቁን ምንቸት ጣድና ለእነዚህ ሰዎች ወጥ ሥራላቸው” አለው።

39. ከእነርሱም አንዱ ቅጠላ ቅጠል ለማምጣት ወደ ሜዳ ወጥቶ፤ ዱር በቀል ሐረግ አገኘ፤ ከሐረጉም ላይ የቅል ፍሬ ለቅሞ በልብሱ ሙሉ ይዞ ተመለሰና ቈራርጦ በወጡ ምንቸት ውስጥ ጨመረው፤ ምን እንደሆን ግን ማንም አላወቀም።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ 2 ነገሥት 4