ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ማቴዎስ 27:1-17 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

1. ጠዋት በማለዳ ላይ፣ የካህናት አለቆችና የሕዝብ ሽማግሌዎች ሁሉ ኢየሱስ ስለሚገደልበት ሁኔታ ተመካከሩ፤

2. ካሰሩትም በኋላ ወስደው ለገዥው ለጲላጦስ አሳልፈው ሰጡት።

3. አሳልፎ የሰጠው ይሁዳም ኢየሱስ እንደ ተፈረደበት ባየ ጊዜ ተጸጸተ፤ የወሰደውን ሠላሳ ጥሬ ብር ለካህናት አለቆችና ለሕዝቡ ሽማግሌዎች መልሶ በመስጠት፣

4. “ንጹሕ ሰው አሳልፌ በመስጠቴ በድያለሁ” አለ።እነርሱም፣ “ታዲያ እኛ ምን አገባን፤ የራስህ ጕዳይ ነው!” አሉት።

5. ስለዚህ ይሁዳ ብሩን በቤተ መቅደስ ውስጥ ወርውሮ ወጣ፤ ሄዶም ራሱን ሰቅሎ ሞተ።

6. የካህናት አለቆች ብሩን አንሥተው፣ “የደም ዋጋ ስለ ሆነ ወደ መባ ልንጨምረው አይፈቀድም” አሉ፤

7. ተመካክረውም ለእንግዶች የመቃብር ስፍራ እንዲሆን በገንዘቡ የሸክላ ሠሪውን ቦታ ገዙበት።

8. ስለዚህም ያ ቦታ እስከ ዛሬ ድረስ “የደም መሬት” ተብሎ ይጠራል።

9. በዚህም በነቢዩ ኤርምያስ እንዲህ ተብሎ የተነገረው ተፈጸመ፤ “ለእርሱ ዋጋ ይሆን ዘንድ የእስራኤል ልጆች የገመቱትን ሠላሳ ጥሬ ብር ተቀበሉ፤

10. እግዚአብሔርም ባዘዘኝ መሠረት ለሸክላ ሠሪው ቦታ ከፈሉ።”

11. በዚህ ጊዜ ኢየሱስ አገረ ገዥው ፊት ቀረበ፤ አገረ ገዥውም፣ “አንተ የአይሁድ ንጉሥ ነህን?” በማለት ጠየቀው።ኢየሱስም፣ “አንተው እንዳልኸው ነው” ሲል መለሰለት።

12. የካህናት አለቆችና ሽማግሌዎች ሲከሱት ግን ምንም መልስ አልሰጠም።

13. በዚህ ጊዜ ጲላጦስ፣ “ስንት ነገር አቅርበው እንደሚከሱህ አትሰማምን?” አለው።

14. እርሱ ግን አገረ ገዥው እስኪገረም ድረስ ለቀረበበት ክስ አንዲት ቃል እንኳ አልመለሰም።

15. አገረ ገዥው ሕዝቡ በበዓሉ እንዲፈታላቸው የሚጠይቁትን አንድ እስረኛ የመፍታት ልማድ ነበረው።

16. በዚያን ጊዜ በዐመፅ የታወቀ በርባን የሚባል እስረኛ ነበር።

17. ሕዝቡ እንደተሰበሰቡ ጲላጦስ፣ “ከበርባንና ክርስቶስ ከሚባለው ከኢየሱስ፣ ማንን እንድፈታላችሁ ትፈልጋላችሁ?” አላቸው፤

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ ማቴዎስ 27