ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ሐዋርያት ሥራ 3:6-24 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

6. ጴጥሮስ ግን፣ “እኔ ብርና ወርቅ የለኝም፤ ነገር ግን ያለኝን እሰጥሃለሁ፤ በናዝሬቱ በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ተነሥተህ በእግርህ ተመላለስ” አለው፤

7. ቀኝ እጁንም ይዞ አስነሣው፤ ወዲያውም እግሩና ቊርጭምጭሚቱ በረታ፤

8. ዘሎም ቀጥ ብሎ ቆመ፤ መራመድም ጀመረ፤ ወዲህ ወዲያ እየሄደና እየዘለለም እግዚአብሔርንም እያመሰገነ ከእነርሱ ጋር ወደ ቤተ መቅደሱ አደባባይ ገባ።

9. ሕዝቡም ሁሉ እየተራመደና እግዚአብሔርን እያመሰገነ ሲመላለስ ባዩት ጊዜ፣

10. ይህ ሰው ቀደም ሲል ‘ውብ’ በተባለው የቤተ መቅደስ መግቢያ በር ላይ ተቀምጦ ምጽዋት ይለምን የነበረው እርሱ መሆኑን ዐወቁ፤ በእርሱ ላይ ከተፈጸመውም ነገር የተነሣ በመደነቅና በመገረም ተሞሉ።

11. የተፈወሰውም ለማኝ ከጴጥሮስና ዮሐንስ ጋር ጥብቅ ብሎ አብሮአቸው ሳለ፣ ሕዝቡ ሁሉ በመገረም እነርሱ ወደነበሩበት ‘የሰሎሞን መመላለሻ’ ወደተባለው ስፍራ እየሮጡ መጡ።

12. ጴጥሮስም ይህን ባየ ጊዜ እንዲህ አላቸው፤ “የእስራኤል ሕዝብ ሆይ፤ በዚህ ለምን ትደነቃላችሁ? ደግሞም በእኛ ኀይል ወይም በእኛ ጽድቅ ይህ ሰው ድኖ እንዲመላለስ እንዳደረግነው በመቊጠር፣ ለምን ወደ እኛ አትኵራችሁ ትመለከታላችሁ?

13. የአባቶቻችን አምላክ፣ የአብርሃም፣ የይስሐቅና የያዕቆብ አምላክ ብላቴናውን ኢየሱስን አከበረው፤ እናንተ ግን እንዲሞት አሳልፋችሁ ሰጣችሁት፤ ጲላጦስ ሊፈታው ቢፈልግም እናንተ በእርሱ ፊት ካዳችሁት፤

14. ቅዱሱንና ጻድቁን ክዳችሁ ነፍሰ ገዳዩ እንዲፈታላችሁ ለመናችሁ፤

15. የሕይወት መገኛ የሆነውን ገደላችሁት፤ እግዚአብሔር ግን ከሙታን አስነሣው፤ እኛም ለዚህ ምስክሮች ነን።

16. ይህ የምታዩትና የምታውቁት ሰው የበረታው በኢየሱስ ስም በማመን ነው፤ ሁላችሁም እንደምታዩት ፍጹም ፈውስ እንዲያገኝ ያደረገው የኢየሱስ ስምና በእርሱ አማካይነት የሚገኘው እምነት ነው።

17. “አሁንም ወንድሞች ሆይ፤ እናንተ ይህን ያደረጋችሁት እንደ አለቆቻችሁ ሁሉ ባለማወቅ እንደሆነ ዐውቃለሁ።

18. እግዚአብሔር ግን የእርሱ የሆነው ክርስቶስ መከራን እንዲቀበል አስቀድሞ በነቢያቱ ሁሉ አፍ የተናገረውን ፈጽሞአል።

19. እንግዲህ ኀጢአታችሁ እንዲደመሰስ ንስሓ ግቡ፤ ከመንገዳችሁም ተመለሱ፤ ከጌታም ዘንድ የመታደስ ዘመን ይመጣላችኋል፤

20. ደግሞም አስቀድሞ ለእናንተ የተመደበውን ክርስቶስን እርሱም ኢየሱስን ይልክላችኋል።

21. እግዚአብሔር አስቀድሞ በቅዱሳን ነቢያቱ አፍ እንደ ተናገረ፣ ሁሉን ነገር እስከሚያድስበት ዘመን ድረስ እርሱ በሰማይ ይቈይ ዘንድ ይገባል።

22. ሙሴም እንዲህ ብሎአል፤ ‘ጌታ አምላካችሁ ከእናንተው መካከል እንደ እኔ ያለ ነቢይ ያስነሣላችኋል፤ እርሱ የሚነግራችሁን ሁሉ ስሙት፤

23. ይህን ነቢይ የማትሰማ ነፍስ ሁሉ ከሕዝቡ መካከል ተለይታ ትጥፋ።’

24. “በርግጥም ከሳሙኤል ጀምሮ የተነሱት ነቢያት ሁሉ ስለ እነዚህ ጊዜያት ተናግረዋል።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ ሐዋርያት ሥራ 3