ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ሐዋርያት ሥራ 25:16-27 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

16. “እኔም፣ ተከሳሽ በከሳሾቹ ፊት ቆሞ ለተከሰሰበት ነገር መልስ ለመስጠት ዕድል ሳያገኝ፣ አሳልፎ መስጠት የሮማውያን ልማድ እንዳልሆነ ነገርኋቸው።

17. ስለዚህ ከሳሾቹ ከእኔ ጋር ወደዚህ በመጡ ጊዜ፣ ጒዳዩን ሳላጓትት በማግስቱ ችሎት ተቀምጬ ያን ሰው እንዲያቀርቡት አዘዝሁ።

18. ከሳሾቹም ተነሥተው በመቆም ሲናገሩ፣ እኔ ያሰብሁትን ያህል ከባድ ክስ አላቀረ ቡበትም፤

19. ይልቁን ስለ ገዛ ሃይማኖታቸውና ሞቶ ስለ ነበረው፣ ጳውሎስ ግን ሕያው ነው ስለሚለው ሰው፣ ስለ ኢየሱስ ይከራከሩት ነበር።

20. እኔም ይህን ነገር እንዴት እንደምፈታው ግራ ስለገባኝ፣ ወደ ኢየሩሳሌም ሄዶ ስለ ዚሁ ጒዳይ እንዲፋረድ ፈቃደኝነቱን ጠየቅሁት።

21. ነገር ግን ጳውሎስ ጒዳዩ በንጉሠ ነገሥቱ እንዲታይለት ይግባኝ ባለ ጊዜ፣ እኔም ወደ ቄሳር እስከምልከው ድረስ እስር ቤት እንዲይ አዘዝሁ።”

22. አግሪጳም ፊስጦስን፣ “እኔም እኮ ይህ ሰው ሲናገር መስማት እፈልግ ነበር” አለው።እርሱም፣ “እንግዲያውስ ነገ ትሰማዋለህ” አለው።

23. በማግስቱም አግሪጳና በርኒቄ በታላቅ ክብር መጥተው፣ ከከፍተኛ መኰንኖችና ከከተማዪቱ ታላላቅ ሰዎች ጋር ወደ መሰብሰቢያው አዳራሽ ገቡ፤ በፊስጦስም ትእዛዝ ጳውሎስ እንዲቀርብ ተደረገ።

24. በዚህ ጊዜ ፊስጦስ እንዲህ አለ፤ “ንጉሥ አግሪጳ ሆይ፤ እንዲሁም እዚህ አብራችሁን ያላችሁ ሁሉ፤ ይህን ሰው ታዩታላችሁ? በኢየሩሳሌምና እዚህ በቂሳርያም የሚኖሩ አይሁድ ሁሉ፣ ይህ ሰው ከእንግዲህ በሕይወት መኖር አይገባውም በማለት እየጮኹ ለመኑ።

25. እኔም ለሞት የሚያበቃ አንዳች ነገር አለ ማድረጉን ተረዳሁ፤ ሆኖም ወደ ንጉሠ ነገሥቱ ይግባኝ በማለቱ ወደ ሮም ልልከው ወሰንሁ።

26. ነገር ግን ስለ እርሱ ወደ ጌታዬ የምጽፈው የተረጋገጠ ነገር አላገኘሁም፤ ስለዚህም ከተመረመረ በኋላ የምጽፈውን ነገር ለማግኘት ሁላችሁም ፊት በተለይ ደግሞ ንጉሥ አግሪጳ ሆይ፤ በአንተ ፊት አቀረብሁት፤

27. ይኸውም አንድ እስረኛ ወደ በላይ ሲላክ የተከሰሰበትን ምክንያት አለመግለጽ ትክክል ስላልመሰለኝ ነው።”

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ ሐዋርያት ሥራ 25