ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ሐዋርያት ሥራ 2:25-41 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

25. ዳዊትም ስለ እርሱ እንዲህ ይላል፤“ ‘ጌታን ሁል ጊዜ በፊቴ አየዋለሁ፤እርሱ በቀኜ ነውና፣ከቶ አልታወክም።

26. ስለዚህ ልቤ ደስ አለው፤ አንደበቴም ሐሤት አደረገ፤ሥጋዬም በተስፋ ይኖራል።

27. ነፍሴን በሲኦል አትተዋትምና፤ቅዱስህም መበስበስን እንዲያይ አታደርግም።

28. የሕይወትን መንገድ እንዳውቅ አደረግኸኝ፤በፊትህም በሐሤት ትሞላኛለህ።’

29. “ወንድሞች ሆይ፤ ከቀደምት አባቶች ዳዊት ሞቶ እንደ ተቀበረ፣ መቃብሩም እስከ ዛሬ ድረስ በመካከላችን እንደሚገኝ በድፍረት መናገር እችላለሁ።

30. ነቢይ በመሆኑም፣ እግዚአብሔር ከዘሮቹ አንዱን በዙፋኑ ላይ እንደሚያስቀምጥ በመሐላ ቃል የገባለት መሆኑን ዐወቀ።

31. ይህንን አስቀድሞ በማየቱ እርሱ በሲኦል እንደማይቀርና ሥጋውም እንደማይበሰብስ ስለ ክርስቶስ ትንሣኤ ተናገረ።

32. ይህን ኢየሱስ፣ እግዚአብሔር ከሞት አስነሣው፤ እኛም ሁላችን ለዚህ ነገር ምስክሮች ነን።

33. ስለዚህ በእግዚአብሔር ቀኝ ከፍ ከፍ ካለ በኋላ፣ የመንፈስ ቅዱስን ተስፋ ከአብ ተቀብሎ አሁን የምታዩትንና የምትሰሙትን አፈሰሰው።

34. ዳዊት ወደ ሰማያት አልወጣም፤እርሱ ራሱ ግን እንዲህ ብሎአል፤“ ‘ጌታ ጌታዬን፣

35. “ጠላቶችህን ለእግርህ መረገጫ እስከማደርግልህ ድረስ፣በቀኜ ተቀመጥ” አለው።’

36. “እንግዲህ፣ እግዚአብሔር ይህን እናንተ የሰቀላችሁትን ኢየሱስን፣ ጌታም ክርስቶስም እንዳደረገው የእስራኤል ወገን ሁሉ ይረዳ!”

37. ሕዝቡም ይህን በሰሙ ጊዜ ልባቸው እጅግ ተነካ፤ ጴጥሮስንና ሌሎቹንም ሐዋርያት፣ “ወንድሞች ሆይ፤ ታዲያ ምን እናድርግ?” አሏቸው።

38. ጴጥሮስም እንዲህ አላቸው፤ “ንስሓ ግቡ፤ ኀጢአታችሁም እንዲሰረይላችሁ፣ እያንዳንዳችሁ በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ተጠመቁ፤ የመንፈስ ቅዱስንም ስጦታ ትቀበላላችሁ።

39. የተስፋው ቃል ለእናንተና ለልጆቻችሁ እንዲሁም ጌታ አምላካችን ወደ ራሱ ለሚጠራቸው፣ በሩቅ ላሉትም ሁሉ ነውና።”

40. በሌላ ብዙ ቃል እየመሰከረላቸው፣ “ከዚህ ጠማማ ትውልድ ራሳችሁን አድኑ” በማለት አስጠነቀቃቸው።

41. ቃሉን የተቀበሉትም ተጠመቁ፤ በዚያ ቀን ሦስት ሺህ ያህል ሰዎች በቍጥራቸው ላይ ተጨመሩ።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ ሐዋርያት ሥራ 2