ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ሐዋርያት ሥራ 15:13-26 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

13. እነርሱም ተናግረው ሲጨርሱ፣ ያዕቆብ ተነሥቶ በመቆም እንዲህ አለ፤ “ወንድሞች ሆይ፤ ስሙኝ፤

14. እግዚአብሔር ከአሕዛብ ወገን ለእርሱ የሚሆነውን ሕዝብ አስቀድሞ እንዴት እንደ ጐበኘ ስምዖን አስረድቶናል።

15. እንዲህ ተብሎ የተጻፈው የነቢያቱም ቃል ከዚህ ጋር ይስማማል፤

16. “ ‘ከዚህ በኋላ እመለሳለሁ፤የፈረሰውን የዳዊትን ቤት እገነባለሁ።ፍርስራሹን መልሼ አቆማለሁ፤እንደ ገናም እሠራዋለሁ፤

17. ይኸውም የቀሩት ሰዎች ጌታን እንዲፈልጉ፣ስሜን የተሸከሙ አሕዛብም እንዲሹኝ ነው፤እነዚህን ያደረገ ጌታ እንዲህ ይላል፤’

18. እነርሱም ከጥንት ጀምሮ የታወቁ ናቸው።

19. “ስለዚህ ወደ እግዚአብሔር የተመለሱትን አሕዛብ እንዳናስጨንቃቸው ይህ የእኔ ብያኔ ነው።

20. ይልቁን በጣዖት ከረከሰ ነገር፣ ከዝሙት ርኵሰት፣ ታንቆ የሞተ እንስሳ ሥጋ ከመብላትና ደም ከመመገብ እንዲርቁ ልንጽፍላቸው ይገባል፤

21. የሙሴ ሕግማ ከጥንት ጀምሮ በየሰንበቱ በምኵራብ ሲነበብና በየከተማው ሲሰበክ ኖሮአልና።”

22. በዚህ ጊዜ ሐዋርያትና ሽማግሌዎች ከመላው ቤተ ክርስቲያን ጋር ሆነው ከመካከላቸው አንዳንድ ሰዎችን መርጠው፣ ከጳውሎስና ከበርንባስ ጋር ወደ አንጾኪያ ለመላክ ወሰኑ፤ ከወንድሞችም መካከል ዋነኛ የነበሩትን በርስያን የተባለውን ይሁዳንና ሲላስን መረጡ፤

23. በእነርሱም እጅ ቀጥሎ ያለውን ደብዳቤ ላኩ፤ወንድሞቻችሁ ከሆኑት ከሐዋርያትና ከሽማግሌዎች፤ከአሕዛብ ወገን አምነው በአንጾኪያ፣ በሶሪያና በኪልቅያ ለሚገኙ ወንድሞች፤ሰላምታችን ይድረሳችሁ።

24. አንዳንድ ሰዎች ያለ እኛ ፈቃድ ከእኛ ዘንድ ወጥተው በንግግራቸው ልባችሁን እንዳወኩና እንዳናወጧችሁ ሰምተናል።

25. ስለዚህ ጥቂት ሰዎች መርጠን ከተወዳጆቹ ከበርናባስና ከጳውሎስ ጋር ወደ እናንተ ለመላክ ሁላችንም ተስማምተናል፤

26. በርናባስና ጳውሎስም ስለ ጌታችን ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ ስም ሕይወታቸውን አሳልፈው የሰጡ ናቸው።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ ሐዋርያት ሥራ 15