ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ሉቃስ 3:3-12 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

3. እርሱም ለኀጢአት ስርየት የሚሆን የንስሓን ጥምቀት እየሰበከ በዮርዳኖስ ወንዝ አካባቢ ወዳሉት ስፍራዎች ሁሉ መጣ፤

4. ይኸውም ነቢዩ ኢሳይያስ በመጽሐፉ እንዲህ ሲል በጻፈው ቃል መሠረት ነበር፤“በበረሓ እንዲህ ብሎ የሚጮኽ ሰው ድምፅ፤‘የጌታን መንገድ አዘጋጁ፤ጐዳናውንም አቅኑ፤

5. ሸለቆው ሁሉ ይሞላል፤ተራራውና ኰረብታው ሁሉ ዝቅ ይላል፤ጠማማው መንገድ ቀና፣ሸካራውም ጐዳና ትክክል ይሆናል፤

6. የሰውም ዘር ሁሉ የእግዚአብሔርን ማዳን ያያል።’ ”

7. ዮሐንስም በእርሱ እጅ ሊጠመቁ የወጡትን ሰዎች እንዲህ ይላቸው ነበር፤ “እናንት የእፉኝት ልጆች፣ ከሚመጣው ቍጣ እንድትሸሹ ማን መከራችሁ?

8. እንግዲህ ለንስሓ የሚገባ ፍሬ አፍሩ፤ ደግሞም በልባችሁ፣ ‘አብርሃም አባታችን አለን’ ማለትን አትጀምሩ፤ እግዚአብሔር ከእነዚህ ድንጋዮች ለአብርሃም ልጆች ማስነሣት እንደሚችል እነግራችኋለሁና።

9. አሁን እንኳ ምሳር በዛፎች ሥር ተቀምጦአል፤ መልካም ፍሬ የማያፈራም ዛፍ ሁሉ ተቈርጦ ወደ እሳት ይጣላል።”

10. ሕዝቡም፣ “ታዲያ፣ ምን እናድርግ?” ብለው ጠየቁት።

11. ዮሐንስም፣ “ሁለት ልብስ ያለው ምንም ለሌለው ያካፍል፤ ምግብ ያለውም እንዲሁ ያድርግ” ብሎ መለሰላቸው።

12. ቀረጥ ሰብሳቢዎችም ሊጠመቁ ወደ እርሱ መጥተው፣ “መምህር ሆይ፤ እኛስ ምን እናድርግ?” አሉት።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ ሉቃስ 3