ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ሉቃስ 3:10-28 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

10. ሕዝቡም፣ “ታዲያ፣ ምን እናድርግ?” ብለው ጠየቁት።

11. ዮሐንስም፣ “ሁለት ልብስ ያለው ምንም ለሌለው ያካፍል፤ ምግብ ያለውም እንዲሁ ያድርግ” ብሎ መለሰላቸው።

12. ቀረጥ ሰብሳቢዎችም ሊጠመቁ ወደ እርሱ መጥተው፣ “መምህር ሆይ፤ እኛስ ምን እናድርግ?” አሉት።

13. እርሱም፣ “ከታዘዛችሁት በላይ ቀረጥ አትሰብስቡ” አላቸው።

14. ወታደሮች ደግሞ፣ “እኛስ ምን እናድርግ?” ብለው ጠየቁት።እርሱም፣ “የማንንም ገንዘብ በግፍ አትንጠቁ፤ ሰውንም በሐሰት አትክሰሱ፤ ደመወዛችሁ ይብቃችሁ” አላቸው።

15. ሕዝቡ በጒጒት እየተጠባበቁ ሳሉ፣ “እርሱ ክርስቶስ ይሆንን?” እያሉ ሁሉም በልባቸው ስለ ዮሐንስ ያሰላስሉ ነበር።

16. ዮሐንስ ለሁሉም እንዲህ ሲል መለሰላቸው፤ “እኔ በውሃ አጠምቃችኋለሁ፤ ነገር ግን ከእኔ የሚበረታ ይመጣል፤ እኔም የእርሱን የጫማ ማሰሪያ መፍታት የሚገባኝ አይደለሁም፤ እርሱ በመንፈስ ቅዱስና በእሳት ያጠምቃችኋል፤

17. ዐውድማውን ፈጽሞ ለማጥራትና ስንዴውንም ወደ ጐተራው ለመክተት መንሹ በእጁ ነው፤ ገለባውን ግን በማይጠፋ እሳት ያቃጥለዋል።”

18. ዮሐንስም በብዙ ሌሎች የምክር ቃላት ሕዝቡን እያስጠነቀቀ ወንጌልን ሰበከላቸው።

19. ነገር ግን ዮሐንስ፣ የአራተኛውን ክፍል ገዥ ሄሮድስን የወንድሙ ሚስት በነበረችው በሄሮድያዳ ምክንያትና ስለ ሌሎች ሥራዎቹ በገሠጸው ጊዜ፣

20. ሄሮድስ ይህን በሌላው ሁሉ ላይ በመጨመር፣ ዮሐንስን ወህኒ ቤት አስገባው።

21. ሕዝቡ ሁሉ ከተጠመቀ በኋላ ኢየሱስም ተጠመቀ፤ እየጸለየም ሳለ ሰማይ ተከፈተ፤

22. መንፈስ ቅዱስም በአካላዊ ቅርጽ እንደ ርግብ በእርሱ ላይ ወረደ፤ ከሰማይም፣ “የምወድህ ልጄ አንተ ነህ፤ በአንተ ደስ ይለኛል” የሚል ድምፅ መጣ።

23. ኢየሱስ አገልግሎቱን ሲጀምር ዕድሜው ሠላሳ ዓመት ያህል ነበር፤ ሕዝቡም እንደ መሰላቸው የዮሴፍ ልጅ ሆኖ፣የኤሊ ልጅ፣

24. የማቲ ልጅ፣የሌዊ ልጅ፣ የሚልኪ ልጅ፣የዮና ልጅ፣ የዮሴፍ ልጅ፣

25. የማታትዩ ልጅ፣ የአሞጽ ልጅ፣የናሆም ልጅ፣ የኤሲሊም ልጅ፣የናጌ ልጅ፣

26. የማአት ልጅ፣የማታትዩ ልጅ፣ የሴሜይ ልጅ፣የዮሴፍ ልጅ፣ የዮዳ ልጅ፣

27. የዮናን ልጅ፣ የሬስ ልጅ፣የዘሩባቤል ልጅ፣ የሰላትያል ልጅ፣የኔሪ ልጅ፣

28. የሚልኪ ልጅ፣የሐዲ ልጅ፣ የዮሳስ ልጅ፣ የቆሳም ልጅ፣የኤልሞዳም ልጅ፣ የኤር ልጅ፣

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ ሉቃስ 3