ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

2 ጢሞቴዎስ 1:3-10 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

3. ሳላቋርጥ ሌሊትና ቀን በጸሎቴ ስለ አንተ ሳስብ፣ ቀደምት አባቶች እንዳደረጉት በንጹሕ ኅሊና የማመልከውን እግዚአብሔርን አመሰግናለሁ።

4. እንባህን እያስታወስሁ በደስታ እሞላ ዘንድ ላይህ እናፍቃለሁ።

5. ግብዝነት የሌለበት እምነትህን አስታውሳለሁ፤ ይህ እምነት ቀድሞ በአያትህ በሎይድ እንዲሁም በእናትህ በኤውንቄ ዘንድ ነበረ፤ አሁን ደግሞ በአንተ እንዳለ ተረድቻለሁ።

6. ስለዚህ በእጆቼ መጫን የተቀበልኸውን በአንተ ውስጥ ያለውን የእግዚአብሔርን ስጦታ እንድታቀጣጥል አሳስብሃለሁ፤

7. እግዚአብሔር የኀይልና የፍቅር፣ ራስንም የመግዛት መንፈስ እንጂ የፍርሀት መንፈስ አልሰጠንምና።

8. እንግዲህ፣ ስለ ጌታችን ለመመስከር ወይም የእርሱ እስረኛ በሆንሁት በእኔ አትፈር፤ ነገር ግን በእግዚአብሔር ኀይል ስለ ወንጌል ከእኔ ጋር መከራን ተቀበል፤

9. እኛ ስላደረግነው አንዳች ነገር ሳይሆን ከዕቅዱና ከጸጋው የተነሣ ያዳነን ወደ ቅዱስ ሕይወትም የጠራን እርሱ ነው። ይህም ጸጋ ከዘላለም ዘመናት በፊት በክርስቶስ ኢየሱስ ተሰጠን፤

10. አሁን ግን ሞትን ደምስሶ በወንጌል አማካይነት ሕይወትንና ኢመዋቲነትን ወደ ብርሃን ባወጣው በመድኀኒታችን በክርስቶስ ኢየሱስ መምጣት ተገልጦአል።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ 2 ጢሞቴዎስ 1