ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ዘፍጥረት 4:3-20 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

3. በአንድ ወቅት፣ ቃየን ከምድር ፍሬ ለእግዚአብሔር (ያህዌ) መሥዋዕት አቀረበ።

4. አቤልም መጀመሪያ ከተወለዱት በጎች መካከል ስባቸውን መሥዋዕት አድርጎ አቀረበ። እግዚአብሔር (ያህዌ) ወደ አቤልና ወደ መሥዋዕቱ ተመለከተ፤

5. በቃየንና በመሥዋዕቱ ግን አልተደሰተም፤ ስለዚህ ቃየን ክፉኛ ተናደደ፤ ፊቱም ጠቈረ።

6. እግዚአብሔር አምላክም (ያህዌ ኤሎሂም) ቃየንን እንዲህ አለው፤ “ለምን ተናደድህ? ለምንስ ፊትህ ጠቈረ?

7. መልካም ብታደርግ ተቀባይነትን አታገኝምን? መልካም ባታደርግ ግን፣ ኀጢአት በደጅህ እያደባች ናት፤ ልታሸንፍህ ትፈልጋለች፤ አንተ ግን ተቈጣጠራት።”

8. ቃየንም ወንድሙን አቤልን፣ “እስቲ ና፤ ወደ መስኩ እንውጣ” አለው፤ በመስኩም ሳሉ፣ ቃየን ወንድሙን አቤልን አጠቃው፤ ገደለውም።

9. ከዚያም፣ እግዚአብሔር (ያህዌ) ቃየንን፣ “ወንድምህ አቤል የት ነው?” አለው።ቃየንም፣ “አላውቅም፤ እኔ የወንድሜ ጠባቂ ነኝን?” ሲል መለሰ።

10. እግዚአብሔርም (ያህዌ) እንዲህ አለ፤ “ምንድ ነው ያደረግኸው? ስማ! የወንድምህ ደም ከምድር ወደ እኔ ይጮኻል።

11. እንግዲህ የተረገምህ ነህ፤ የወንድምህን ደም ከእጅህ ለመቀበል አፏን ከከፈተችው መሬት ትሰደዳለህ።

12. ብታርሳትም ፍሬዋን አትለግስህም፤ በምድር ላይ ኰብላይና ተንከራታች ትሆናለህ።”

13. ቃየንም እግዚአብሔርን (ያህዌ) እንዲህ አለው፤ “ቅጣቴ ልሸከመው ከምችለው በላይ ነው።

14. እነሆ፤ ዛሬ ከምድሪቱ አባረርኸኝ፤ ከፊትህም እሸሸጋለሁ፤ በምድር ላይ ኰብላይና ተንከራታች እሆናለሁ፤ የሚያገኘኝም ሁሉ ይገድለኛል።”

15. እግዚአብሔር (ያህዌ) ግን፣ “የለም! እንደርሱ አይሆንም፤ ማንም ቃየንን ቢገድል፣ ሰባት ዕጥፍ የበቀል ቅጣት ይቀበላል” አለው፤ ስለዚህ፣ ያገኘው ሁሉ እንዳይገድለው እግዚአብሔር (ያህዌ) በቃየን ላይ ምልክት አደረገለት።

16. ቃየንም ከእግዚአብሔር (ያህዌ) ፊት ወጥቶ ሄዶ፣ ከዔድን በስተ ምሥራቅ በምትገኝ ኖድ በተባለች ምድር ተቀመጠ።

17. ቃየን ሚስቱን ተገናኛት፤ እርሷም ፀንሳ ሄኖክን ወለደች። ቃየን የቈረቈረውን ከተማ በልጁ ስም ሄኖክ ብሎ ጠራው።

18. ሄኖክ ኢራድን ወለደ፤ ኢራድም መሑያኤልን፣ መሑያኤልም ማቱሣኤልን፣ ማቱሣኤልም ላሜሕን ወለደ።

19. ላሜሕ ሁለት ሚስቶች አገባ፤ የአንደኛዋ ስም ዓዳ፣ የሁለተኛዋም ጺላ ነበር።

20. ዓዳ ያባልን ወለደች፤ እርሱም በድንኳን ለሚኖሩ ከብት አርቢዎች አባት ነበረ።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ ዘፍጥረት 4