ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ዘፍጥረት 27:26-35 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

26. ከዚያም አባቱ ይስሐቅ፣ ያዕቆብን፣ “ልጄ ሆይ፤ እስቲ ቀረብ በልና ሳመኝ” አለው።

27. ያዕቆብም ቀርቦ ሳመው፤ ይስሐቅ የያዕቆብን ልብስ ካሸተተ በኋላ እንዲህ ብሎ መረቀው፤“እነሆ፤ የልጄ ጠረን፣ እግዚአብሔር (ያህዌ) እንደ ባረከው፣እንደ መስክ መዐዛ ነው።

28. እግዚአብሔር (ኤሎሂም) የሰማይን ጠል፣የምድርንም በረከት፣የተትረፈረፈ እህልና የወይን ጠጅ ይስጥህ።

29. መንግሥታት ይገዙልህ፤ሕዝቦችም ተደፍተው እጅ ይንሡህ፤የወንድሞችህ ጌታ ሁን፤የእናትህም ልጆች ተደፍተው እጅ ይንሡህ፤የሚረግሙህ የተረገሙ ይሁኑ፤የሚባርኩህ የተባረኩ ይሁኑ።”

30. ይስሐቅ ያዕቆብን መርቆ እንዳበቃ፣ ያዕቆብ ገና ከአባቱ ዘንድ ሳይወጣ ወዲያውኑ፣ ወንድሙ ዔሳው ከዐደን ተመለሰ።

31. እርሱም ደግሞ ጣፋጭ ምግብ በማዘጋጀት ለአባቱ አቅርቦ፣ “አባቴ ሆይ፤ እንድትመርቀኝ፣ እስቲ ቀና በልና ካደንሁት ብላ” አለው።

32. አባቱ ይስሐቅም፣ “አንተ ደግሞ ማን ነህ?” ሲል ጠየቀው። እርሱም፣ “እኔማ የበኵር ልጅህ ዔሳው ነኝ” አለው።

33. በዚህ ጊዜ ይስሐቅ ክፉኛ እየተንቀጠቀጠ፣ “ታዲያ ቀደም ሲል አድኖ ያመጣልኝ ማን ነበር? አንተ ከመምጣትህ በፊት በልቼ መረቅሁት፤ እርሱም በእርግጥ የተባረከ ይሆናል” አለው።

34. ዔሳው የአባቱን ቃል ሲሰማ፣ ድምፁን ከፍ በማድረግ ምርር ብሎ አለቀሰ፤ አባቱንም፣ “አባቴ ሆይ፤ እኔንም ደግሞ እባክህ መርቀኝ” አለው።

35. ይስሐቅም፣ “ወንድምህ መጥቶ አታሎኝ ምርቃትህን ወስዶብሃል” አለው።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ ዘፍጥረት 27