ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ዘፀአት 39:6-22 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

6. የከበሩ መረግዶችን በወርቅ ፈርጦች በመክፈፍ፣ እንደ ማኅተም የእስራኤልን ልጆች ስሞች ቀረጹባቸው።

7. ከዚያም እግዚአብሔር (ያህዌ) ሙሴን እንዳዘዘው በኤፉዱ የትከሻ ንጣዮች ላይ ለእስራኤል ልጆች እንደ መታሰቢያ ድንጋዮች አያያዟቸው።

8. የደረት ኪሱንም ጥበበኛ ባለ ሙያ እንደሚሠራው ሥራ በተመሳሳይ መንገድ ሠሩት፤ እንደ ኤፉዱም ከወርቅ፣ ከሰማያዊ፣ ከሐምራዊና ከቀይ ማግ በቀጭኑም ከተፈተለ በፍታ ሠሩት።

9. ርዝመቱ አንድ ስንዝር ወርዱም አንድ ስንዝር ሲሆን፣ ጥንድ ድርብ ሆኖ ባለ አራት ማእዘን ነበረ።

10. ከዚያም የከበሩ ድንጋዮችን በአራት ረድፍ በላዩ ላይ አደረጉበት፤ በመጀመሪያው ረድፍ ሰርድዮን፣ ቶጳዝዮንና የሚያብረቀርቅ ዕንቍ ነበር፤

11. በሁለተኛውም ረድፍ በሉር፣ ሰንፔርና አልማዝ፣

12. በሦስተኛውም ረድፍ ያክንት፣ ኬልቄዶንና አሜቴስጢኖስ፣

13. በአራተኛውም ረድፍ ቢረሌ፣ መረግድና ኢያስጲድ ነበረ፤ በወርቅ ፈርጥ ላይ ተደርገው ነበር።

14. ለእያንዳንዱ የእስራኤል ልጆች ስም አንዳንድ ሆኖ፣ በእያንዳንዱ ላይ እንደ ማኅተም ከዐሥራ ሁለቱ ነገዶች የአንዱ ስም የተቀረጸበት ዐሥራ ሁለት ድንጋዮች ነበሩ።

15. ለደረት ኪሱም ልክ እንደ ገመድ ከንጹሕ ወርቅ የተጐነጐኑ ድሪዎችን አበጁለት።

16. ሁለት የወርቅ ፈርጦችንና ሁለት የወርቅ ቀለበቶችን ሠርተው ቀለበቶቹን ከደረት ኪሱ ሁለት ጐኖች ጋር አያያዟቸው።

17. ሁለቱን የወርቅ ድሪዎች በደረት ኪሱ ጐንና ጐን ካሉት ቀለበቶች ጋር አያያዟቸው፤

18. የድሪዎቹን ሌሎች ጫፎች ከፊት ካለው ከኤፉዱ የትከሻ ንጣዮች ጋር በማገናኘት ከሁለቱ የወርቅ ፈርጦች ጋር አያያዟቸው።

19. ሁለት የወርቅ ቀለበቶችን ሠርተው ከኤፉዱ ቀጥሎ ካሉት ከሌሎቹ ሁለት የደረት ኪስ ጐኖች ጋር ከውስጠኛው ጠርዝ ላይ አያያዟቸው።

20. ከዚያም ሁለት ተጨማሪ የወርቅ ቀለበቶችን ሠርተው ልክ ከኤፉዱ መታጠቂያ በላይ፣ ከመጋጠሚያው አጠገብ፣ ከኤፉዱ ፊት ለፊት ካሉት ከትከሻ ንጣዮች ጋር አያያዟቸው።

21. እግዚአብሔር (ያህዌ) ሙሴን እንዳዘዘው የደረት ኪሱ ከኤፉዱ ተነጥሎ ለብቻው እንዳይንጠለጠል የደረት ኪሱን ቀለበቶች ከመታጠቂያው ጋር በማገናኘት፣ ከኤፉዱ ቀለበቶች ጋር በሰማያዊ ፈትል አሠሯቸው።

22. የኤፉዱን ቀሚስ በሸማኔ ሥራ ሙሉ በሙሉ ከሰማያዊ ጨርቅ ሠሩት፤

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ ዘፀአት 39