ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ዘፀአት 28:15-35 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

15. “የፍርድ መስጫውን የደረት ኪስ ብልኅ ሠራተኛ እንደሚሠራው አድርገህ አብጀው፤ ልክ እንደ ኤፉዱ ከወርቅ፣ ከሐምራዊ፣ ከቀይ ማግና በቀጭኑ ከተፈተለ በፍታ አብጀው።

16. ርዝመቱ አንድ ስንዝር፣ ስፋቱ አንድ ስንዝር ሆኖ ባለ አራት ማእዘንና በድርቡ የታጠፈ ይሁን።

17. ከዚያም በላዩ ላይ በአራት ረድፍ የከበሩ ድንጋዮች አድርግበት፤ በመጀመሪያው ረድፍ ሰርዲዮን፣ ቶጳዝዮን፣ የሚያበረቀርቅ ዕንቁ፤

18. በሁለተኛውም ረድፍ በሉር፣ ሰንፔር፣ አልማዝ፤

19. በሦስተኛው ረድፍ ያክንት፣ ኬልቄዶን፣ አሜቴስጢኖስ፤

20. በአራተኛውም ረድፍ ቢረሌ፣ መረግድና ኢያስጴድ አድርግበት፤ በወርቅ ፈርጥም ክፈፋቸው።

21. የዐሥራ ሁለቱ ነገዶች ስሞች እንደ ማኅተም የተቀረጸባቸው ለእያንዳንዱ የእስራኤል ልጆች ስም ዐሥራ ሁለት ድንጋዮች ይሁኑ።

22. “ለደረት ኪሱ ከንጹሕ ወርቅ እንደ ገመድ ሆኖ የተጌጠ ጒንጒን አብጅለት።

23. ለእርሱም ሁለት የወርቅ ቀለበቶች አብጅተህ ከደረት ኪሱ ሁለት ጎኖች ጋር አያይዘው።

24. ሁለቱን የወርቅ ጒንጒኖች በደረት ኪሱ ጐኖች ላይ ካሉት ቀለበቶች ጋር አያይዛቸው።

25. ሌሎቹን የጒንጒን ጫፎች በፊት ላይ ካለው ኤፉድ በትከሻው ላይ ካሉት ንጣዮች ጋር በማጋጠም ከሁለቱ የወርቅ ፈርጦች ጋር አያይዛቸው።

26. ሁለት የወርቅ ቀለበቶች አበጅተህ ከኤፉዱ ቀጥሎ ባለው በውስጠኛ ጠርዝ ላይ፣ በሌላ በኩል ካሉት ሁለት የደረት ኪስ ጒኖች ጋር አያይዛቸው።

27. ሁለት ተጨማሪ የወርቅ ቀለበቶች አበጅተህ ከኤፉዱ መታጠቂያ ከፍ ብሎ ከመጋጠሚያው አጠገብ ካለው በኤፉዱ ፊት ለፊት፣ በትከሻ ላይ ካሉት ንጣዮች ግርጌ ጋር አያይዘው።

28. የደረት ኪሱም ቀለበቶች፣ የደረት ኪሱ ከኤፉዱ ጋር እንዳይላቀቅ፣ ከመታጠቂያው ጋር በማገናኘት በሰማያዊ ገመድ ከኤፉዱ ቀለበቶች ጋር ይያያዙ።

29. “አሮን ወደ መቅደሱ በሚገባበት ጊዜ በእግዚአብሔር (ያህዌ) ፊት ለዘላለም መታሰቢያ ይሆን ዘንድ የእስራኤልን ልጆች ስሞች በፍርድ መስጫው ደረት ኪስ በልቡ ላይ ይሸከም።

30. ወደ እግዚአብሔር (ያህዌ) ፊት በሚገባበት ጊዜ በአሮን ልብ ላይ ይሆኑ ዘንድ ኡሪሙንና ቱሚሙን በደረት ኪሱ አድርግ፤ ስለዚህ አሮን ሁል ጊዜ ለእስራኤላውያን የፍርድ መስጫውን በእግዚአብሔር (ያህዌ) ፊት በልቡ ላይ ይሸከማል።

31. “የኤፉዱ ቀሚስ ሙሉ በሙሉ ከሰማያዊ ጨርቅ ይሁን፤

32. ከላይ በኩል በመካከሉ ዐንገትጌ አድርገህ አብጀው፤ እንዳይቀደድም በማስገቢያው ዙሪያ እንደ ክሳድ ያለ ዝምዝም ጠርዝ ሥራለት።

33. በጨርቁ ጠርዝ ዙሪያ ከሰማያዊ፣ ከሐምራዊና ከቀይ ማግ ሮማኖቹን፣ በመካከሉም የወርቅ ሻኵራዎችን አብጅ።

34. የወርቅ ሻኵራዎቹና ሮማኖቹ በጨርቁ ጠርዝ ዙሪያ በመፈራረቅ ይሆናሉ።

35. አሮንም በአገልግሎቱ ጊዜ ይህን መልበስ አለበት፤ በእግዚአብሔር (ያህዌ) ፊት ወደ መቅደሱ በገባና ከመቅደሱ ሲወጣ እንዳይሞት የሻኵራዎቹ ድምፅ ይሰማል።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ ዘፀአት 28