ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ዘፀአት 28:14-27 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

14. እንደ ገመድ ያሉ ሁለት በንጹሕ ወርቅ የተጐነጐኑ ድሪዎችን አብጅተህ ከፈርጡ ጋር አያይዛቸው።

15. “የፍርድ መስጫውን የደረት ኪስ ብልኅ ሠራተኛ እንደሚሠራው አድርገህ አብጀው፤ ልክ እንደ ኤፉዱ ከወርቅ፣ ከሐምራዊ፣ ከቀይ ማግና በቀጭኑ ከተፈተለ በፍታ አብጀው።

16. ርዝመቱ አንድ ስንዝር፣ ስፋቱ አንድ ስንዝር ሆኖ ባለ አራት ማእዘንና በድርቡ የታጠፈ ይሁን።

17. ከዚያም በላዩ ላይ በአራት ረድፍ የከበሩ ድንጋዮች አድርግበት፤ በመጀመሪያው ረድፍ ሰርዲዮን፣ ቶጳዝዮን፣ የሚያበረቀርቅ ዕንቁ፤

18. በሁለተኛውም ረድፍ በሉር፣ ሰንፔር፣ አልማዝ፤

19. በሦስተኛው ረድፍ ያክንት፣ ኬልቄዶን፣ አሜቴስጢኖስ፤

20. በአራተኛውም ረድፍ ቢረሌ፣ መረግድና ኢያስጴድ አድርግበት፤ በወርቅ ፈርጥም ክፈፋቸው።

21. የዐሥራ ሁለቱ ነገዶች ስሞች እንደ ማኅተም የተቀረጸባቸው ለእያንዳንዱ የእስራኤል ልጆች ስም ዐሥራ ሁለት ድንጋዮች ይሁኑ።

22. “ለደረት ኪሱ ከንጹሕ ወርቅ እንደ ገመድ ሆኖ የተጌጠ ጒንጒን አብጅለት።

23. ለእርሱም ሁለት የወርቅ ቀለበቶች አብጅተህ ከደረት ኪሱ ሁለት ጎኖች ጋር አያይዘው።

24. ሁለቱን የወርቅ ጒንጒኖች በደረት ኪሱ ጐኖች ላይ ካሉት ቀለበቶች ጋር አያይዛቸው።

25. ሌሎቹን የጒንጒን ጫፎች በፊት ላይ ካለው ኤፉድ በትከሻው ላይ ካሉት ንጣዮች ጋር በማጋጠም ከሁለቱ የወርቅ ፈርጦች ጋር አያይዛቸው።

26. ሁለት የወርቅ ቀለበቶች አበጅተህ ከኤፉዱ ቀጥሎ ባለው በውስጠኛ ጠርዝ ላይ፣ በሌላ በኩል ካሉት ሁለት የደረት ኪስ ጒኖች ጋር አያይዛቸው።

27. ሁለት ተጨማሪ የወርቅ ቀለበቶች አበጅተህ ከኤፉዱ መታጠቂያ ከፍ ብሎ ከመጋጠሚያው አጠገብ ካለው በኤፉዱ ፊት ለፊት፣ በትከሻ ላይ ካሉት ንጣዮች ግርጌ ጋር አያይዘው።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ ዘፀአት 28