ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ዘፀአት 15:5-20 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

5. ቀላያትንም ለበሱ፤እንደ ድንጋይ ወደ ጥልቁ ወረዱ።

6. “አቤቱ እግዚአብሔር (ያህዌ) ሆይ፤ቀኝ እጅህ በግርማ ከበረ፤አቤቱ እግዚአብሔር (ያህዌ) ሆይ፤ቀኝ እጅህ ጠላትን አደቀቀ።

7. በግርማህ ታላቅነት፣የተቃወሙህን ጣልኻቸው፤ቍጣህን ሰደድህ፤እንደ ገለባም በላቸው።

8. በአፍንጫህ እስትንፋስ፣ውሆች ተቈለሉ፤ፈሳሾችም እንደ ግድግዳ ቆሙ፤የጥልቁ ውሃ ባሕሩ ውስጥ ረጋ።

9. “ጠላት፣ ‘አሳድዳቸዋለሁ፤እማርካቸዋለሁ፤ምርኮን እካፈላለሁ፤ነፍሴ በእነርሱ ትጠግባለች፤ሰይፌን እመዛለሁ፤እጄም ትደመስሳቸዋለች አለ።

10. አንተ ግን እስትንፋስህን አነፈስህ፤ባሕርም ከደናቸው፤በኀያላን ውሆች፣እንደ ብረት ሰጠሙ።

11. “አቤቱ እግዚአብሔር (ያህዌ) ሆይ፤ከአማልክት መካከል፣ እንደ አንተ ማን አለ?በቅድስናው የከበረ፣በክብሩ የሚያስፈራ፣ድንቆችን የሚያደርግ፣እንደ አንተ ማን አለ?

12. ቀኝ እጅህን ዘረጋህ፤ምድርም ዋጠቻቸው።

13. ‘በማይለወጠው ፍቅርህ፣የተቤዥሃቸው ሕዝብህን ትመራለህ፤እነርሱን በብርታትህ፣ወደ ቅዱስ ማደሪያህ ትመራቸዋለህ።

14. አሕዛብ ይሰማሉ፤ ይንቀጠቀጡማል፤የፍልስጥኤምን ሕዝብ ሥቃይ ይይዛቸዋል።

15. የኤዶምም አለቆች ይርዳሉ፤የሞአብ አለቆች በእንቅጥቃጤ ይያዛሉ፤የከነዓን ሕዝብ ይቀልጣሉ።

16. አቤቱ እግዚአብሔር (ያህዌ) ሆይ፤ ሕዝብህእስከሚያልፉ ድረስ፣የተቤዠኻቸው ሕዝብህ እስኪያልፉ ድረስ፣ድንጋጤና ሽብር በእነርሱ ላይ ይመጣል፤በክንድህ ብርታት፣እንደ ድንጋይ የማይንቀሳቀሱ ይሆናሉ።

17. እግዚአብሔር (ያህዌ) ሆይ፤ ማደሪያህእንዲሆን በሠራኸው ስፍራ፣ጌታ (አዶናይ) ሆይ፤ እጆችህ በሠሩት መቅደስ፣በርስትህ ተራራ ላይ፣ ታመጣቸዋለህ፤ ትተክላቸዋለህም።

18. እግዚአብሔር (ያህዌ)፣ከዘላለም እስከ ዘላለም ይነግሣል።”

19. የፈርዖን ፈረሶች፣ ሠረገሎቹና ፈረሰኞቹ ወደ ባሕሩ በገቡ ጊዜ እግዚአብሔር (ያህዌ) የባሕሩን ውሃ በላያቸው ላይ መለሰባቸው፤ እስራኤላውያን ግን በባሕሩ ውስጥ በደረቅ ምድር ተሻገሩ።

20. ከዚያም የአሮን እኅት ነቢይቱ ማርያም ከበሮዋን አንሥታ ያዘች፤ የቀሩትም ሴቶች ሁሉ ከበሮ ይዘው እያሸበሸቡ ተከተሏት።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ ዘፀአት 15