ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ዘኁልቍ 27:1-11 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

1. የምናሴ ልጅ፣ የማኪር ልጅ፣ የገለዓድ ልጅ፣ የአፌር ልጅ፣ የሰለጰዓድ ሴት ልጆች ከዮሴፍ ልጅ ከምናሴ ጐሣዎች ነበሩ፤ ስማቸውም ማህለህ፣ ኑዓ፣ ዔግላ፣ ሚልካና ቲርጻ ይባላል። እነርሱም፣

2. ወደ መገናኛው ድንኳን መግቢያ ቀረቡ፤ በሙሴ፣ በካህኑ በአልዓዛር፣ በመሪዎችና በመላው ማኅበርም ፊት ቆመው እንዲህ አሉ፤

3. “አባታችን በምድረ በዳ ሞተ፤ ተባብረው በእግዚአብሔር (ያህዌ) ላይ ካመፁት ከቆሬ ተከታዮች ጋር አልነበረም፤ የሞተው ግን በራሱ ኀጢአት ሲሆን፣ ወንዶች ልጆችም አልነበሩትም።

4. ታዲያ አባታችን ወንድ ልጅ ባለመውለዱ ስሙ ከጐሣዎቹ ተለይቶ እንዴት ይጠፋል? ለእኛም በአባታችን ዘመዶች መካከል ርስት ስጡን።”

5. ስለዚህ ሙሴ ጒዳያቸውን ወደ እግዚአብሔር (ያህዌ) አቀረበ፤

6. እግዚአብሔርም (ያህዌ) እንዲህ አለው፤

7. “የሰለጰዓድ ልጆች ጥያቄ ትክክል ነው፤ በእርግጥ በአባታቸው ዘመዶች መካከል ድርሻቸውን ርስት አድርገህ ልትሰጣቸው ስለሚገባ የአባታቸውን ድርሻ ለእነርሱ አስተላልፍላቸው።

8. “እስራኤላውያንን እንዲህ በላቸው፤ ‘አንድ ሰው ወንድ ልጅ ሳይተካ ቢሞት ውርሱን ለሴት ልጁ አስተላልፉ።

9. ሴት ልጅ ከሌለችው ደግሞ ውርሱን ለወንድሞቹ ስጡ።

10. ወንድሞች ከሌሉትም ውርሱን ለአባቱ ወንድሞች ስጡ።

11. አባቱ ወንድሞች ከሌሉትውርሱ ከጐሣው መካከል ቅርብ ለሆነ ዘመዱ ይሰጥ፤ እርሱም ይውረሰው። ይህም እግዚአብሔር (ያህዌ) ሙሴን ባዘዘው መሠረት ለእስራኤላውያን ሕጋዊ መመሪያ ይሆናቸዋል።’ ”

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ ዘኁልቍ 27