ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ዘሌዋውያን 24:5-12 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

5. “የላመ ዱቄት ወስደህ ዐሥራ ሁለት ኅብስት ጋግር፤ እያንዳንዱ ኅብስትም በሁለት ዐሥረኛ የኢፍ መስፈሪያ ዱቄት ይጋገር።

6. እነዚህንም ስድስት ስድስቱን በሁለት ረድፍ በእግዚአብሔር (ያህዌ) ፊት ባለው የንጹሕ ወርቅ ጠረጴዛ ላይ አኑራቸው።

7. ከኅብስቱ ጋር የመታሰቢያ ድርሻ ሆኖ ለእግዚአብሔር (ያህዌ) በእሳት የሚቀርብ መሥዋዕት እንዲሆን ንጹሕ ዕጣን በእያንዳንዱ ረድፍ ላይ አኑር።

8. ኅብስቱ የእስራኤልን ሕዝብ ይወክል ዘንድ ዘወትር በየሰንበቱ በእግዚአብሔር (ያህዌ) ፊት ይደርደር፤ ይህም የዘላለም ቃል ኪዳን ነው።

9. ኅብስቱ የአሮንና የልጆቹ ድርሻ ነው፤ በተቀደሰ ስፍራም ይበሉታል፤ ለእግዚአብሔር (ያህዌ) በእሳት ከሚቀርበው መሥዋዕት እጅግ የተቀደሰ ድርሻቸው ነውና።”

10. እናቱ እስራኤላዊት፣ አባቱ ግብፃዊ የሆነ አንድ ሰው በእስራኤላውያን መካከል ወጣ፤ በሰፈርም ውስጥ ከአንድ እስራኤላዊ ጋር ተጣሉ።

11. የእስራኤላዊቱ ልጅ የእግዚአብሔርን (ያህዌ) ስም በማቃለል ሰደበ፤ ስለዚህም ወደ ሙሴ አመጡት፤ የሰውየው እናት ስም ሰሎሚት ነበር፤ እርሷም ከዳን ወገን የተወለደው የደብራይ ልጅ ነበረች።

12. የእግዚአብሔር (ያህዌ) ፈቃድም ግልጽ እስኪሆንላቸው ድረስ በግዞት አኖሩት።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ ዘሌዋውያን 24