ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ዕዝራ 5:10-17 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

10. የመሪዎቻቸውን ስም በጽሑፍ እናሳውቅህ ዘንድ ስማቸውን ደግሞ ጠየቅን።

11. የሰጡን መልስ ይህ ነው፤“እኛ የሰማይና የምድር አምላክ አገልጋዮች ነን፤ አሁንም እንደ ገና የምንሠራው ቤተ መቅደስ፣ ከብዙ ዘመናት በፊት ታላቁ የእስራኤል ንጉሥ ሠርቶ የጨረሰውን ነው።

12. ነገር ግን አባቶቻችን የሰማይን አምላክ አስቈጥተውት ስለ ነበር፣ ለባቢሎኑ ንጉሥ ለከለዳዊው ናቡከደነፆር አሳልፎ ሰጣቸው፤ እርሱም ይህን ቤተ መቅደስ አፈራርሶ ሕዝቡን ወደ ባቢሎን አፈለሰ።

13. “ይሁንና ቂሮስ፣ የባቢሎን ንጉሥ በሆነ በመጀመሪያው ዓመት ይህን የእግዚአብሔር ቤት እንደ ገና እንዲሠሩ ንጉሥ ቂሮስ ትእዛዝ ሰጠ።

14. ናቡከደነፆር ከኢየሩሳሌም ቤተ መቅደስ አውጥቶ ባቢሎን በሚገኘው ቤተ መቅደስ ውስጥ ያኖራቸውን የእግዚአብሔርን ቤት የወርቅና የብር ዕቃዎች ከባቢሎን ቤተ መቅደስ አስመጣ።“ከዚያም ንጉሥ ቂሮስ፣ አገረ ገዥ አድርጎ ለሾመውና ሰሳብሳር ተብሎ ለሚጠራው ሰው ሰጠው፤

15. ቀጥሎም፣ ‘እነዚህን ዕቃዎች ይዘህ ሂድና በኢየሩሳሌም ቤተ መቅደስ ውስጥ አኑራቸው፤ የእግዚአሔር ቤት ቀድሞ በነበረበት ቦታ እንደ ገና ይሠራ’ አለው።

16. ስለዚህ ይህ ሰሳብሳር መጥቶ በኢየሩሳሌም የሚገኘውን የእግዚአብሔርን ቤተ መቅደስ መሠረት ጣለ፤ ከዚያን ቀን ጀምሮ እስከ ዛሬ ድረስ እነሆ በመሠራት ላይ ነው፤ ሆኖም ገና አላለቀም።

17. “አሁንም ንጉሡን ደስ የሚያሰኘው ቢሆን፣ ይህ የእግዚአብሔር ቤት በኢየሩሳሌም እንዲሠራ ንጉሥ ቂሮስ በርግጥ ትእዛዝ ሰጥቶ እንደሆነ በባቢሎን ቤተ መንግሥት ግምጃ ቤት የተቀመጡት መዛግብት እንዲመረመሩ ያድርግ፤ ከዚያም ንጉሡ ስለዚህ ጒዳይ የወሰነውን ይላክልን።”

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ ዕዝራ 5