ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ኤርምያስ 9:16-26 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

16. እነርሱንም ሆነ አባቶቻቸውን በማያውቋቸው ሕዝቦች መካከል እበትናቸዋለሁ፤ እስካጠፋቸውም ድረስ በሰይፍ አሳድዳቸዋለሁ።”

17. የሰራዊት ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፤“እንግዲህ፤ አልቃሽ ሴቶች ጥሩ፤ሥልጡን ሙሾ አውራጆች አስመጡ፤

18. እነርሱ ፈጥነው ይምጡ፤ዐይኖቻችን እንባ እስኪያጐርፉ፣ሽፋሽፍቶቻችንም ውሃ እስኪያመነጩ፣ስለ እኛ ሙሾ ያውርዱልን።

19. እነሆ የዋይታ ድምፅ ከጽዮን ተሰምቶአል፤ እንዲህም ይላል፤‘ምንኛ ወደቅን!ውርደታችንስ እንዴት ታላቅ ነው!ቤቶቻችን ፈራርሰዋልና፤አገራችንን ጥለን እንሂድ።’ ”

20. እናንት ሴቶች ሆይ፤ የእግዚአብሔርን ቃል ስሙ፤ጆሮቻችሁን ከአንደበቱ ለሚወጡት ቃላት ክፈቱ፤ሴቶች ልጆቻችሁን ዋይታ፣አንዳችሁም ሌላውን ሙሾ አስተምሩ።

21. ሞት በመስኮቶቻችን ገብቶአል፤ወደ ምሽጎቻችንም ዘልቆአል፤ሕፃናትን ከየመንገዱ፣ወጣቶችን ከየአደባባዩ ጠራርጎ ወስዶአል።

22. እንዲህ በሉ፤ “እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፤“ ‘የሰዎች ሬሳ፣በሜዳ እንደተጣለ ጒድፍ፣ማንም እንደማይሰበስበው፣ከዐጫጅ ኋላ እንደተተወ ቃርሚያ ይወድቃል።’ ”

23. እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፤“ጥበበኛ በጥበቡ አይታበይ፤ኀያልም በኀይሉ አይመካ፤ሀብታምም በሀብቱ አይኵራራ፤

24. የሚመካ ግን፣እኔ እግዚአብሔር እንደሆንሁ በማወቁና፣በምድር ላይ ምሕረትን፣ ፍትሕንና ጽድቅን የማደርግ መሆኔን በመረዳቱ፣በዚህ ይመካ፤ እኔ በእነዚህ ነገሮች፣እደሰታለሁና፤”ይላል እግዚአብሔር።

25. እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፤ “ሥጋቸውን ብቻ የተገረዙትን ሁሉ የምቀጣበት ጊዜ ይመጣል፤

26. እነርሱም ግብፅ፣ ይሁዳ፣ ኤዶም፣ አሞን፣ ሞዓብና ጠጒራቸው ዙሪያውን የሚከረከም የበረሓ ነዋሪዎች ሁሉ ናቸው፤ እነዚህ ሕዝቦች ሁሉ በርግጥ የተገረዙ አይደሉምና፤ የእስራኤልም ቤት ሁሉ ልባቸው አልተገረዘም።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ ኤርምያስ 9