ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ኤርምያስ 49:12-21 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

12. እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፤ “ከጽዋው መጠጣት የማይገባቸው ሊጠጡ ግድ ከሆነ፣ አንተ እንዴት ሳትቀጣ ትቀራለህ? መቀጣትህ አይቀርም፤ መጠጣት ይገባሃል።

13. ባሶራ ፈራርሳ የድንጋጤ፣ የመዘባበቻና የርግማን ምልክት እንደምትሆን በራሴ ምያለሁ” ይላል እግዚአብሔር፤ “ከተሞቿም ሁሉ ለዘላለም ባድማ ይሆናሉ።”

14. ከእግዚአብሔር ዘንድ መልእክት ሰምቻለሁ፤“እርሷን ለመውጋት ተሰብሰቡ፤ለጦርነትም ውጡ”የሚል መልእክተኛ ወደ ሕዝቦች ተልኮአል።

15. “እነሆ፤ በሕዝቦች መካከል ታናሽ፣በሰዎችም ዘንድ የተናቅህ አደርግሃለሁ።

16. አንተ በዐለት ንቃቃት ውስጥ የምትኖር፣የተራራውንም ከፍታ የያዝህ ሆይ፤የምትነዛው ሽብር፣የልብህም ኵራት አታሎሃል፤መኖሪያህን እንደ ንስር በከፍታ ቦታ ብትሠራም፣ከዚያ ወደ ታች እጥልሃለሁ፤”ይላል እግዚአብሔር።

17. “ኤዶም የድንጋጤ ምልክት ትሆናለች፤ከቍስሎቿም ሁሉ የተነሣ፣በዚያ የሚያልፍ ሁሉ በመደነቅ ያላግጥባታል።”

18. በዙሪያቸው ካሉት ከተሞች ጋር፣ሰዶምና ገሞራ እንደ ተገለበጡ፣”ይላል እግዚአብሔር፤እንዲሁ ማንም በዚያ አይኖርም፤አንድም ሰው አይቀመጥባትም።

19. “አንበሳ ከዮርዳኖስ ደኖች፣ወደ ግጦሽ ሜዳ ብቅ እንደሚል፣እኔም በኤዶም ላይ ድንገት እወጣለሁ፤ ከምድሩም አባርረዋለሁ።የመረጥሁትን በእርሱ ላይ እሾማለሁ፤እንደ እኔ ያለ ማን ነው? ማንስ ሊገዳደረኝ ይችላል?የትኛውስ እረኛ ሊቋቋመኝ ይችላል?

20. ስለዚህ እግዚአብሔር በኤዶም ላይ ያለውን ዕቅድ፣በቴማን በሚኖሩትም ላይ ያሰበውን አሳብ ስሙ፤ታናናሹ መንጋ ተጐትቶ ይወሰዳል፤በእነርሱም ምክንያት መሰማሪያቸውን ፈጽሞ ያጠፋል።

21. በውድቀታቸው ድምፅ ምድር ትናወጣለች፤ጩኸታቸውም እስከ ቀይ ባሕር ያስተጋባል።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ ኤርምያስ 49