ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ኤርምያስ 25:12-27 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

12. “ነገር ግን ሰባው ዓመት ከተፈጸመ በኋላ፣ የባቢሎንን ንጉሥና ሕዝቡን፣ የባቢሎናውያንንም ምድር ስለ በደላቸው እቀጣቸዋለሁ” ይላል እግዚአብሔር፤ “ለዘላለምም ባድማ አደርጋታለሁ፤

13. በምድሪቱ ላይ የተናገርሁትን ሁሉ ይኸውም በዚህ መጽሐፍ የተጻፈውንና ኤርምያስ በሕዝቦች ሁሉ ላይ የተናገረውን ትንቢት አመጣባታለሁ።

14. ሕዝቧም ለብዙ ሕዝቦችና ለታላላቅ ነገሥታት ባሮች ይሆናሉ፤ እንደ አድራጎታቸውና እንደ እጃቸውም ሥራ እከፍላቸዋለሁ።”

15. የእስራኤል አምላክ እግዚአብሔር እንዲህ አለኝ፤ “በቍጣዬ የወይን ጠጅ የተሞላውን ይህን ጽዋ ከእጄ ውሰድ፤ እኔ ወደ ምልክህም ሕዝቦች ሁሉ ሄደህ አጠጣቸው።

16. በጠጡም ጊዜ ይንገዳገዳሉ፤ በመካከላቸው ከምሰደው ሰይፍ የተነሣ ያብዳሉ።”

17. ስለዚህ ጽዋውን ከእግዚአብሔር እጅ ተቀብዬ እርሱ ወደ ላከኝ ሕዝቦች ሁሉ ሄድሁ፤ እንዲጠጡትም አደረግሁ፤

18. ዛሬ እንደሆነው ሁሉ ባድማና ሰዎች የሚጸየፉአቸው መዘባበቻና ርግማን እንዲሆኑ፦ ኢየሩሳሌምንና የይሁዳን ከተሞች፣ ነገሥታቷንና ባለሥልጣኖቿን፣

19. የግብፅን ንጉሥ ፈርዖንን፣ አገልጋዮቹን፣ ባለሥልጣኖቹንና ሕዝቡን ሁሉ፣

20. በዚያ የሚኖሩትን ድብልቅ ሕዝብ ሁሉ፣ የዖፅ ምድር ነገሥታትን ሁሉ፣ በአስቀሎና፣ በጋዛ፣ በአቃሮንና በአዛጦንም ሕዝብ ቅሬታ ያሉትን የፍልስጥኤም ነገሥታት፣

21. ኤዶምን፣ ሞዓብን፣ አሞንን፣

22. የጢሮስንና የሲዶናን ነገሥታት ሁሉ፣ ከባሕሩ ማዶ ያሉ የጠረፍ ምድር ነገሥታትን፣

23. ድዳንን፣ ቴማንን፣ ቡዝን፣ ጠጒራቸውን ዙሪያውን የሚከረከሙትን ሕዝብ ሁሉ፣

24. የዐረብ ነገሥታትን ሁሉ፣ በምድረ በዳ የሚኖሩትን የድብልቅ ሕዝብ ነገሥታት ሁሉ፣

25. የዘምሪ፣ የኤላምና የሜዶን ነገሥታትን ሁሉ፣

26. በቅርብና በሩቅ ያሉትን የሰሜን ነገሥታትንም ሁሉ በማከታተል፣ በምድር ላይ ያሉትን መንግሥታት ሁሉ አጠጣኋቸው፤ ከእነዚህም ሁሉ በኋላ የሺሻክ ንጉሥ ደግሞ ይጠጣል።

27. “አንተም እንዲህ ብለህ ንገራቸው፤ ‘የእስራኤል አምላክ የሰራዊት ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፦ ጠጡ፤ ስከሩ፤ አስታውኩም፤ ዳግመኛም ላትነሡ በመካከላችሁ በምሰደው ሰይፍ ፊት ውደቁ።’

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ ኤርምያስ 25