ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ኤርምያስ 1:1-12 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

1. የኬልቅያስ ልጅ፣ ኤርምያስ የተናገረው ቃል ይህ ነው፤ አባቱ በብንያም አገር በዓናቶት ከሚገኙት ካህናት አንዱ ነበረ።

2. የእግዚአብሔር ቃል የይሁዳ ንጉሥ፣ የአሞን ልጅ ኢዮስያስ በነገሠ በዐሥራ ሦስተኛው ዓመት ወደ ኤርምያስ መጣ፤

3. ደግሞም በይሁዳ ንጉሥ፣ በኢዮስያስ ልጅ በኢዮአቄም ንግሠ ዘመን፤ እንዲሁም በይሁዳ ንጉሥ፣ በኢዮስያስ ልጅ በሴዴቅያስ ንግሠ ዘመን፤ እስከ ዐሥራ አንደኛው ዓመት መጨረሻ ድረስ የኢየሩሳሌም ሕዝብ ተማርኮ እስከ ሄደበት እስከ አምስተኛው ወር ድረስ ወደ እርሱ ይመጣ ነበር።

4. የእግዚአብሔር ቃል ወደ እኔ መጣ፤ እንዲህም አለኝ፤

5. “በማሕፀን ሳልሠራህ ዐወቅሁህ፤ከመወለድህ በፊት ለየሁህ፤ለሕዝቦችም ነቢይ እንድትሆን ሾምሁህ።”

6. እኔም፣ “ጌታ እግዚአብሔር ሆይ፤ እንዴት እንደምናገር አላውቅም፤ ገና ሕፃን ልጅ ነኝና” አልሁ።

7. እግዚአብሔር ግን እንዲህ አለኝ፤ “ ‘ገና ሕፃን ልጅ ነኝ’ አትበል፤ ወደምልክህ ሁሉ ሄደህ፣ ያዘዝሁን ሁሉ ትናገራለህ፤

8. እኔ አድንህ ዘንድ ከአንተ ጋር ነኝና አትፍራቸው” ይላል እግዚአብሔር።

9. እግዚአብሔርም እጁን ዘርግቶ አፌን ዳሰሰና እንዲህ አለኝ፤ “እነሆ፤ ቃሌን በአፍህ አኑሬአለሁ፤

10. እንግዲህ፣ እንድትነቅልና እንድታፈርስ፣ እንድታጠፋና እንድትገለብጥ፣ እንድታንጽና እንድትተክል በአሕዛብና በመንግሥታት ላይ ዛሬ ሾምሁህ።”

11. የእግዚአብሔር ቃል፣ “ኤርምያስ ሆይ፣ ምን ታያለህ?” ሲል ወደ እኔ መጣ።እኔም፣ “የለውዝ በትር አያለሁ” አልሁ።

12. እግዚአብሔርም፣ “ትክክል አይተሃል፤ ቃሌን እፈጽመው ዘንድ እተጋለሁና” አለኝ።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ ኤርምያስ 1