ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ኢዩኤል 2:12-24 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

12. “አሁንም ቢሆን፣በጾም፣ በልቅሶና በሐዘን፣በፍጹም ልባችሁ ወደ እኔ ተመለሱ” ይላል እግዚአብሔር።

13. ልባችሁን እንጂ፣ልብሳችሁን አትቅደዱ፤ወደ አምላካችሁ ወደ እግዚአብሔር ተመለሱ፤እርሱ መሓሪና ርኅሩኅ፣ቊጣው የዘገየና ፍቅሩ የበዛ፣ክፉ ነገር ከማምጣትም የሚታገሥ ነውና።

14. በምሕረቱ ተመልሶ፣ለአምላካችሁ ለእግዚአብሔር የሚሆነውን፣የእህል ቊርባንና የመጠጥ ቊርባን እንዲተርፋችሁ፣በረከቱን ይሰጣችሁ እንደሆነ ማን ያውቃል?

15. በጽዮን መለከትን ንፉ፤ቅዱስ ጾምን ዐውጁ፤የተቀደሰን ጉባኤ ጥሩ።

16. ሕዝቡን ሰብስቡ፤ጉባኤውን ቀድሱ፤ሽማግሌዎችን በአንድነት አቅርቡ፤ሕፃናትን ሰብስቡ፤ጡት የሚጠቡትንም አታስቀሩ፤ሙሽራው እልፍኙን ይተው፣ሙሽሪትም የጫጒላ ቤቷን ትተው።

17. በእግዚአብሔር ፊት የሚያገለግሉ ካህናት፣በመሠዊያውና በቤተ መቅደሱ አደባባይ መካከል ሆነው ያልቅሱ፤እንዲህም ይበሉ፤ “እግዚአብሔር ሆይ፤ ሕዝብህን አድን፤ርስትህን በአሕዛብ መካከል መተረቻ፣መሣቂያና መሣለቂያም አታድርግ፤ለምንስ በሕዝቦች መካከል፣‘አምላካቸው ወዴት ነው?’ ይበሉን።”

18. እነሆ፤ እግዚአብሔር ስለ ምድሩ ይቀናል፤ስለ ሕዝቡም ይራራል።

19. እግዚአብሔርም እንዲህ ሲል ይመልስላቸዋል፤“እህል፣ አዲስ የወይን ጠጅና ዘይት፣እስክትጠግቡ ድረስ እሰጣችኋለሁ፤የሕዝቦች መዘባበቻ አላደርጋችሁም።

20. “የሰሜንን ሰራዊት ከእናንተ አርቃለሁ፤ፊቱን ወደ ምሥራቁ ባሕር፣ጀርባውንም ወደ ምዕራቡ ባሕር በማድረግ፣ወደ ደረቀውና ወደ ባድማው ምድር እገፋዋለሁ፤ግማቱ ይወጣል፤ክርፋቱም ይነሣል።”በእርግጥ እርሱ ታላቅ ነገር አድርጎአል።

21. ምድር ሆይ፤ አትፍሪ፤ደስ ይበልሽ፤ ሐሤትም አድርጊ፤በእርግጥ እግዚአብሔር ታላቅ ነገር አድርጎአል።

22. የዱር እንስሳት ሆይ፤ አትፍሩ፤መሰማሪያ መስኮቹ ለምልመዋልና፤ዛፎቹ ፍሬያቸውን አፍርተዋል፤የበለሱ ዛፍና የወይኑ ተክልም እጅግ አፍርተዋል።

23. የጽዮን ሰዎች ሆይ፤ ደስ ይበላችሁ፤በአምላካችሁ በእግዚአብሔር፣ ሐሤት አድርጉ፤የበልግን ዝናብ፣በጽድቅ ሰጥቶአችኋልና፤እንደ ቀድሞውም፣የበልግንና የጸደይን ዝናብ በብዛት ልኮላችኋል።

24. ዐውድማዎቹ በእህል ይሞላሉ፤መጥመቂያ ጒድጓዶችም፣ በአዲስ የወይን ጠጅና በዘይት ተሞልተው ያፈሳሉ።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ ኢዩኤል 2